21/09/2024
እህታችን የሺ ( ከንፍታሌም የጸሎት ህብረት) ጸሎት በመምራት አገልግላለች። ከ ግሎሪ የአምልኮ ህብረት ጋር ደግሞ በዝማሬ እግዚአብሔርን አምልከናል። ወንድማችን ይስሃቅ አብርሃም የእንግድነት ህይወት በሚል ርዕስ ከ 2ኛ ጴጥሮስ 2፡4-12 የእግዚአብሔርን ቃል አካፍሎናል። በመልዕክቱም ቅዱሳን በምድር ላይ የሚኖረን ቆይታ የእንግድነት ስለሆነ፤ እንዴት መመላለስ እንዳለብን ከክፍሉ አሳይቶናል።
እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት የሚቻለው የልጁን በመምሰል በሚኖር ህይወት ነው።
ቅዱሳን በምድር ላይ ሲኖሩ እንግዳ እንደመሆናቸው ፤ ከስጋዊ ምኞትና ከምድራዊነት በመራቅና ኢየሱስን በመቅረብ፤ ሰማያዊ ቤታቸውን መጠባበቅ አለባቸው።
የቅዱሳን የእንግድነት ህይወት ምን መምሰል አለበት?
1, በኢየሱስ ህያዋን ድንጋይ በመሆን
1ኛ ጴጥሮስ 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁴ በሰውም ወደ ተጣለ በእግዚአብሔር ዘንድ ግን ወደ ተመረጠና ክቡር ወደ ሆነው ወደ ሕያው ድንጋይ ወደ እርሱ እየቀረባችሁ፥
⁵ እናንተ ደግሞ እንደ ሕያዋን ድንጋዮች ሆናችሁ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕትን ታቀርቡ ዘንድ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ።
ይህም ቅዱሳን ኢየሱስን የመምሰል ህይወት ሊኖራቸው እንደሚገባ የሚያሳይ ነው።
2, በኢየሱስ መንፈሳዊ መሥዋዕትና መንፈሳዊ ቤት በመሆን
“እናንተ ደግሞ እንደ ሕያዋን ድንጋዮች ሆናችሁ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕትን ታቀርቡ ዘንድ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ።”
— 1ኛ ጴጥሮስ 2፥5
ይህም ደግሞ ቅድሳን ለእግዚአብሔር የተሰጠና የተለየ ህይወት ሊኖረን እንደሚገባ የሚያሳይ ነው።
3, ከስጋዊ ምኞት በመራቅ
“ወዳጆች ሆይ፥ ነፍስን ከሚዋጋ ሥጋዊ ምኞት ትርቁ ዘንድ እንግዶችና መጻተኞች እንደ መሆናችሁ እለምናችኋለሁ፤”
— 1ኛ ጴጥሮስ 2፥11
4, በአህዛብ መካከል ያለነቀፍና በመልካም ህይወት በመመላለስ
“ስለሚመለከቱት ስለ መልካም ሥራችሁ፥ ክፉ እንደምታደርጉ በዚያ እናንተን በሚያሙበት ነገር፥ በሚጎበኝበት ቀን እግዚአብሔርን ያከብሩት ዘንድ በአሕዛብ መካከል ኑሮአችሁ መልካም ይሁን።”
— 1ኛ ጴጥሮስ 2፥12
በአጠቃላይ እኛ ቅዱሳን ሰማያዊ ቤት ያለን እንደመሆናችን መጠን በምድር ላይ እንግዳና መጻተኛ መሆናችንን ተረድተን፤ ኢየሱስን በመምሰልና ስጋዊ ምኞትን በማስወገድ መንፈሳዊ መሥዋዕትና መንፈሳዊ ቤት ለመሆን መሰራት አለብን።
የአገልግሎት ትምህርት ሲማሩ ለቆዩ ልጆች ሰርተፍኬት ተሰቷቸዋል።
በጥቂቱ የነበረን ፕሮግራም ይህን ይመስላል። በፕሮግራሙ የተሳተፍችሁ ሁሉ እግዚአብሔር ይባርካችሁ። ዘወትር ቅዳሜ ከአመሻሽ 11፡30 ጀምሮ በሐዋሳ መሐል ከተማ ቃለ ሕይወት ቤተክርስቲያን በመገኘት አብረውን የጌታን ጸጋ ይካፈሉ።
የሐ/መ/ከ/ቃ/ሕ/ቤ/ክ የሚዲያ አግልግሎት ክፍል ።
መስከረም 11 2017 ዓ.ም
📸HMKHC MEDIA CREW