28/05/2026
የወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ እጩ ምሩቃን ደቀ መዛሙርት ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቡራኬ ተቀበሉ።
ግንቦት ፳ ፳፻፲፰ ዓ.ም
በብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አባታዊ ምሪት፣ በወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ እጩ ምሩቃን ደቀመዛሙርት ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘንድ ቀርበው ቡራኬ ተቀበሉ
ኮሌጁ ለሁለተኛ ጊዜ የሚያስመርቃቸው እነዚህ ደቀ መዛሙርት፣ ባለፉት ሦስት ተከታታይ ዓመታት በዲፕሎማ መርሐ ግብር የሥነ መለኮቱንና የአብነቱን ትምህርት አስተባብረው የተማሩ ናቸው። ተማሪዎቹ በቆይታቸው የንድፈ ሐሳብ ትምህርት ብቻ ሳይሆን፣ ወደፊት ለሚጠብቃቸው ሰፊ የቤተክርስቲያን አገልግሎት የሚበጅ ተግባራዊ የክህነት ልምምድ እንዲኖራቸው በብፁዕነታቸው ከፍተኛ ጥረት መደረጉ ታውቋል።
የኮሌጁ እጩ ምሩቃን እንደገለጡት፤ ከቃል ስብከት ባለፈ ምሳሌ የሚሆን የአገልግሎት ሕይወት እንዲኖራቸው ተደርጎ መሠራቱና የብፁዕነታቸው የቅርብ ክትትል መኖሩ፣ ወደፊት ለሚኖራቸው መንፈሳዊ ጉዞ ትልቅ ስንቅ እንደሚሆናቸው ገልጸዋል።
ይህ ከቅዱስነታቸው የተገኘው አባታዊ ቡራኬም፣ ተመርቀው ወደ ተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ለአገልግሎት በሚሰማሩበት ወቅት ቤተክርስቲያንን ይበልጥ በጠንካራ መንፈስና በትጋት ለማገልገል ትልቅ ኃይልና መነሳሳትን እንደሚፈጥርላቸው ተማሪዎቹ በደስታ ገልጸዋል።
በዚሁ ታላቅ የቡራኬ መርሐ ግብር ላይ የወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ እጩ ምሩቃንን ጨምሮ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ እና የሐዋሳ ታቦር ፍኖተ ጥበብ መንፈሳዊ ኮሌጅ እጩ ደቀመዛሙርት በጋራ ተገኝተዋል።
የዕለቱ የቡራኬ መርሐ ግብር ከተጠናቀቀ በኋላ፣ የወልቂጤ ቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ እጩ ደቀመዛሙርት ሌላ መንፈሳዊ ጉብኝት አድርገዋል። በዚህም መሠረት ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በነበሩበት ወቅት ያደራጁትን የቦሌ ቡልቡላ አቡነ ተክለሃይማኖት የእናቶች ገዳምን ተዘዋውረው የጎበኙ ሲሆን፣ እዚያም በብፁዕነታቸው የጸሎት ሥነ ሥርዓት ተከናውኖላቸዋል።
@ ሳሌም ሚዲያ ጉራጌ ሀገረ ስብከት/Gurage Diocese ነው
👇👇👇👇👇👇
ፍጡነ ረድኤት የአርባ ምንጭ ደ/ፀ/ቅ/ጊዮርጊስና ደ/ሎ/ቅ/ኪዳነ ምሕረት አቢያተ ክርስቲያናት ሚዲያ