25/07/2026
ብፁዕ አቡነ ኤልያስ በሠገን ከተማ የሚገኘውን የደብረ መዊዕ ቅዱስ ገብርኤል አዲስ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ባረኩ።
የጋሞና አካባቢው፣ ጎፋ እና ባስኬቶ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ኤልያስ፣ ከሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ገሪማ ጌታነህ እና ከሀገረ ስብከቱ ጸሐፊ መጋቤ ሰናያት ያዕቆብ ደስታ ጋር በመሆን በሠገን ከተማ በሚገኘው ደብረ መዊዕ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በመገኘት አዲሱን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ባረኩ።
ብፁዕነታቸውና አባቶች ወደ ስፍራው ሲደርሱ፦ በቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት፣ በሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያን፣ በከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ በሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም በቁጥር በርካታ በሆኑ ምእመናን አቀባበል ተደርጎላቸዋል።
በአቀባበል ሥነ ሥርዓቱ ላይ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ያቀረቡት የምስጋና መዝሙርና የሊቃውንቱ ያሬዳዊ ወረብ ለበዓሉ ልዩ ድምቀት የሰጠ ሲሆን፣ ብፁዕነታቸውም የተጠናቀቀውን አዲስ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ባርከው ለጸሎትና ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።
የወረዳው ቤተ ክህነት አስተዳደር ቀሲስ በፍቃዱ ወልዱ እንዳስታወቀት፣ ነገ ሐምሌ 19 ቀን 2018 ዓ.ም የሚከበረውን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ የንግሥ ክብረ በዓል ምክንያት በማድረግ የታቦተ ሕጉ መውጣት ሥነ ሥርዓት በታላቅ ድምቀት ይካሄዳል።
በዕለቱ የማኅሌት፣ የቅዳሴና የትምህርተ ወንጌል አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን፣ ምእመናን በነቂስ ወጥተው የሊቀ መላእክቱን ቡራኬና ረድኤት እንዲቀበሉ ጥሪ ቀርቧል።