Tewahido Haymanote

Tewahido Haymanote Living It is a spritual page

29/04/2026
29/04/2026

Celebrating my 10th year on Facebook. Thank you for your continuing support. I could never have made it without you. 🙏🤗🎉

ኦ ድንግል በመኑ ወበአምሳለ መኑ ናስተማስለኪድንግል ሆይ በማንና በማን ምሳሌ እንመስልሻለንመግቢያቅድመ ዓለም የነበረ፣ ዓለምን አሳልፎ የሚኖር፣ በምስጋና ባሕር መካከል የሚቀመጥ፣ የባሕርይ ብ...
29/04/2026

ኦ ድንግል በመኑ ወበአምሳለ መኑ ናስተማስለኪ
ድንግል ሆይ በማንና በማን ምሳሌ እንመስልሻለን

መግቢያ
ቅድመ ዓለም የነበረ፣ ዓለምን አሳልፎ የሚኖር፣ በምስጋና ባሕር መካከል የሚቀመጥ፣ የባሕርይ ብርሃን እግዚአብሔር ሆይ! ለዚህ ምሥጢር የሚሆን ልቡናን ስጠን።

​አሁን የምንቆመው በምድራዊ መድረክ ላይ ቢሆንም፣ ሐሳባችን ግን በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም፣ በቅዱሳን መላእክት ማኅበር መካከል ይሁን። እስቲ አዕምሮአችንን ከዚህ ዓለም ግርግር እናውጣው፤ ልባችንን ከመዋለል፣ ነፍሳችንንም ከጭንቀት እናሳርፋት።

​ይህ ድንቅ ምስጋና የሰው ቃል ብቻ አይደለም፤ ነቢያት በሩቅ አይተውት የተረኩት፣ መላእክት በግርምት ያደነቁት፣ ሊቃውንትም በምሥጢር ባሕር ውስጥ ሰጥመው የቀሰሙት ሰማያዊ መና እንጂ። አባታችን ቅዱስ ኤፍሬም "ኦ ድንግል በመኑ ወበአምሳለ መኑ ናስተማስለኪ" ብሎ ሲጀምር፣ መመሰል አቅቶት ሳይሆን፣ የፈጣሪ እናት

የሆነችውን ድንግል ክብር ሲመለከት በአድናቆት ባሕር ውስጥ ስለሰመጠ ነው።

​እኛም አሁን ወደዚህ ምሥጢር ስንገባ፣ እንደ ሙሴ "የቆምህባት ምድር ቅድስት ናትና ጫማህን አውልቅ" የተባለውን እናስተውል፤ የልባችንን የኃጢአትና የጥርጥር ጫማ አውልቀን፣ በትሕትና ሆነን፣ በነቢያት መነጽርነት ያቺን ድንቅ "አምሳለ መለኮት" ድንግልን እንመልከታት።

​ "ኦ ድንግል ምልእተ ውዳሴ በመኑ ወበአምሳለ መኑ ናስተማስለኪ"
​አንቀጸ ንባብ፦ ምስጋና የተመላሽ ድንግል ሆይ! በማንና በምንስ አምሳያ እንመስልሻለን?

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ የድንግል ማርያም ክብር ከፍጡራን ሁሉ በላይ መሆኑን የሚገልጥ ጥያቄ ነው። መመሰልን ለምሳሌ ያህል እንጂ በፍጹም መከካከያ አይደለም።

​ምሥጢር፦ እርሷ "አንቀጸ ብርሃን" ናትና ብርሃንነቷ ከፀሐይ በላይ፣ ንጽሕናዋ ከመላእክት በላይ መሆኑን ያመለክታል።

​ሐተታ፦ "በመኑ" ማለቱ በሰው፣ "በአምሳለ መኑ" ማለቱ በግዑዝ ፍጥረት ነው። ሊቁ "በመኑ" ብሎ መጠየቁ የሚመስላት አጥቶ ሳይሆን፣ ክብሯ ከቃል በላይ መሆኑን ለመግለጥ "አንጽሆ" (ግርምት) መጠቀሙ ነው።

​ለኛ ያለው መልዕክት፦ የእመቤታችንን ክብር ስንናገር በአንደበታችን ሳይሆን በልባችን ትሕትና ሊሆን እንደሚገባ ያስተምረናል።

​ለምሳሌ፦ አንድ ሰው የባሕርን ጥልቀት በጭልፋ ሊለካ እንደማይሞክር ሁሉ፣ የእርሷንም ክብር በሰው አንደበት ተናግሮ መጨረስ አይቻልም።

ውዳሴ ማርያም ዘሰንበት፣ መዝሙረ ዳዊት ፹፮፥፫ (86:3)።
​
"ምዕናም አንቲ ዘእምኔኪ ለብሰ አማኑኤል ልብሰተ ሥጋ ዘኢይተረጐም..."
​አንቀጸ ንባብ፦ ከአንቺ ዘንድ አማኑኤል የማይተረጎም የሥጋን ልብስነት የለበሰብሽ ማደሪያ (መስፈሪያ) አንቺ ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ አማኑኤል ካንቺ ሥጋን ነሳ። ያ ሥጋም እንደ እኛ ሥጋ ከበክለት ሳይሆን ከአዳም ጥንተ ተፈጥሮ የተገኘ ንጹሕ ሥጋ ነው።
​ምሥጢር፦ "ምዕናም" (መስፈሪያ) መባሏ፣ ዓለማት የማይችሉትን አምላክ በማኅፀኗ ስለወሰነችው ነው።

​ሐተታ፦ "ዘኢይተረጐም" ማለቱ የመለኮትና የሥጋ ተዋሕዶ በሰው አዕምሮ የማይመረመር ረቂቅ መሆኑን ለመናገር ነው።

​ለኛ ያለው መልዕክት፦ አምላክ እኛን ለማዳን ሲል ሰው የመሆኑን ትሕትና እናስተውል ዘንድ ነው።
​ለምሳሌ፦ እሳት በብረት ውስጥ ገብቶ ብረቱን ሳያቀልጠው ብረቱ እሳት እንዲሆን፣ መለኮትም በማኅፀኗ ሥጋን ተዋሐደ።
​ዮሐንስ ፩፥፲፬ (1÷14)፣

​ "ወፋእሙኒ ሥጋ ዘአኪ ወመስቄሁ ቃል ለሊሁ ኢየሱስ ክርስቶስ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ ድሩ (ሥጋው) ያንቺ ነው፣ መወርወሪያው (መሸመኛው) ቃል ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ሰሪውም እግዚአብሔር አብ ሲሆን አናሚው (ሸማኔው) መንፈስ ቅዱስ ነው።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ የክርስቶስ ሥጋ የተዘጋጀው በሦስቱ አካላት ሥራ መሆኑን በሸማኔ ምሳሌ ይገልጻል።
​ምሥጢር፦ ተዋሕዶ የሥላሴ ፈቃድና ሥራ ያለበት መሆኑን ያሳያል።
​ሐተታ፦ ሥጋ ካንቺ (ከፈትል) ተገኘ፣ ቃል ደግሞ እንደ መወርወሪያ ሆኖ ሥጋን ተዋሐደ። ይህ የሥጋዌ ምሥጢር ነው።
​ለኛ ያለው መልዕክት፦ ድኅነታችን በሥላሴ ዘንድ የታቀደ ታላቅ ሥራ መሆኑን መረዳት።

​ለምሳሌ፦ አንድ ሸማኔ ፈትልና መወርወሪያን አስተባብሮ ልብስ እንደሚሠራ፣ ሥላሴም ካንቺ ሥጋን ነስተው የሰው ልጅን የድኅነት ልብስ አዘጋጁ።

ሉቃስ ፩፥፴፭
​
"ኦ ዝመንክር ወዕፁብ ዝንቱ ነገር! ኦ ማዕዶት ዘበኀቤኪ ዐደዉ አበው ቀደምት..."
​አንቀጸ ንባብ፦ ይህ ነገር ድንቅና ግሩም ነው! ቀደሞቶቹ አባቶች ከአጥፊው ሞት ወደ ሕይወት የተሻገሩብሽ ድልድይ አንቺ ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ እመቤታችን ከሞት ወደ ሕይወት የምታሻግር ድልድይ ናት።

​ምሥጢር፦ ሔዋን የሞት ምክንያት ስትሆን ማርያም ግን የሕይወት መገኛ ሆና ተገኘች።
​ሐተታ፦ "ማዕዶት" (ድልድይ) መባሏ፣ በበደል ምክንያት ተቋርጦ የነበረውን የሰውና የእግዚአብሔር ግንኙነት በማገናኘቷ ነው።

​ለኛ ያለው መልዕክት፦ ያለ ማርያም አማላጅነትና ሥጋዌ ድኅነት እንዳልተገኘ ማወቅ።
​
ለምሳሌ፦ በወንዝ የተከፈለ ደሴትን ድልድይ እንደሚያገናኘው፣ በኃጢአት የተለየውን ዓለም እርሷ አገናኘችው።
ኤፌሶን ፪፥፲፬

​"ኦ ምዕራግ እምድር እስከ ሰማይ ወብኪ ተሐደሰ ቀዳሚ ኵሉ ፍጥረት"
​አንቀጸ ንባብ፦ ከምድር እስከ ሰማይ የምትደርሺ መሰላል አንቺ ነሽ፤ በአንቺም የቀደመው ፍጥረት ሁሉ ታደሰ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ ያዕቆብ በህልሙ ያያት መሰላል የእመቤታችን ምሳሌ ናት።
​ምሥጢር፦ መላእክት ወደ ምድር የሚወርዱት፣ የሰው ጸሎት ወደ ሰማይ የሚወጣው በአንቺ በኩል ነው ማለት ነው።

​ሐተታ፦ "ተሐደሰ" ማለቱ በአዳም የረከሰውን ተፈጥሮ ክርስቶስ በአንቺ ሥጋን ነስቶ ቀደሰው፣ አደሰው ማለቱ ነው።

​ለኛ ያለው መልዕክት፦ ሰማያዊ ሕይወት የምናገኘው በድንግል ማርያም በኩል መሆኑን ማመን።

​ለምሳሌ፦ ሰማይና ምድርን መሰላል እንደሚያገናኝ፣ እርሷም መለኮትንና ትውልዱን አገናኘች።
​ዘፍጥረት ፳፰፥፲፪

​"አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም... የዋሐቱ ለአቤል..."
​አንቀጸ ንባብ፦ አዳም ከገነት በተሰደደ ጊዜ ተስፋው አንቺ ነሽ፤ በግፍ ለተገደለው ለአቤልም የዋሐቱ ነሽ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ የአዳም ተስፋ "ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ አድንሐለሁ" የተባለው ቃል ፍጻሜው አንቺ ነሽ።
​ምሥጢር፦ የአቤል ደም ይጮህ ነበር፣ የአንቺ ልጅ ደም ግን ይቅርታን ሰጠ።

​ሐተታ፦ ነቢያትና አባቶች ሁሉ ተስፋ የሚያደርጓት እርሷን እንደነበረች ያሳያል።

​ለኛ ያለው መልዕክት፦ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ስንሆን ድንግል ማርያምን ተስፋ እንድናደርግ ነው ተስፋ ያደረጓት ሁሉ በእርሷ ድልድይነት ተሻግረዋል ።
​ለምሳሌ፦ በጨለማ ያለ ሰው ንጋትን ተስፋ እንደሚያደርግ፣ አዳምም በሲኦል ሆኖ አንቺን ተስፋ አደረገ።
​ዘፍጥረት ፫፥፲፭

​"ኄሩቱ ለሴት... ታቦት እንተ ናኅ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የሴት ቸርነቱ፣ የሄኖክ ምግባሩ ነሽ፤ ኖኅ ከጥፋት ውኃ የዳነባት መርከብ አንቺ ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ ኖኅ በታቦት (በመርከብ) ከማየ አይኅ እንደዳነ፣ እኛም በአንቺ ልጅ ከገሃነም እሳት እንድናለን ድነናልም ።
​ምሥጢር፦ መርከቧ ኖኅንና ቤተሰቡን እንደያዘች፣ አንቺም የዓለምን መድኃኒት ያዝሽ።

​ሐተታ፦ የአባቶች ደግነት ሁሉ በአንቺ ላይ ተፈጸመ ማለቱ ነው።
​ለኛ ያለው መልዕክት፦ ዓለም በኃጢአት ማዕበል ስትናወጥ መጠጊያችን ድንግል ማርያም ናት።
​
ለምሳሌ፦ መርከብ በማዕበል መካከል ሆና ሰዎችን እንደምታድን፣ እርሷም በኃጢአት ባህር ውስጥ ለሰመጥን መዳኛችን ናት።
​ዘፍጥረት ፮፥፲፬

"ቡራኬሁ ለሴም... ተናግዶቱ ለአብርሃም... መዓዛሁ ለይስሐቅ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የሴም በረከቱ፣ የአብርሃም እንግድነቱ፣ የይስሐቅ መዓዛው ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ አብርሃም እንግዳ ተቀብሎ በረከት እንዳገኘ፣ በአንቺም ክርስቶስ እንግዳ ሆኖ መጥቶ በረከት ሆነን።
​ምሥጢር፦ የይስሐቅ መዓዛ የተባለችው የልጇ መዓዛ ሕይወት ስለሚሰጥ ነው።
​ሐተታ፦ የአባቶች በረከት ሁሉ ማኅተሟ አንቺ ነሽ።
​ለኛ ያለው መልዕክት፦ በረከት የምናገኘው ከበረከቶች ሁሉ በረከት ከሆነችው ድንግል ነው።
​ዘፍጥረት ፳፯፥፳፯

​ "ወሰዋስዊሁ ለያዕቆብ... ወናዛዚቱ ለዮሴፍ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የያዕቆብ መሰላሉ፣ የዮሴፍ አረጋጊው (ናዛዚው) ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ ዮሴፍ በግብፅ በችግር ጊዜ እንደተረጋጋ፣ ዓለምም በአንቺ ልጅ መምጣት ተረጋጋች።
​ምሥጢር፦ ያዕቆብ መላእክት ሲወጡባት ያያት መሰላል የአንቺ ምሳሌ ናት።

​ለኛ ያለው መልዕክት፦ በሐዘን ጊዜ መጽናኛችን ድንግል ማርያም ናት።
ዘፍጥረት ፴፱

​ "ጸላት ዘሙሴ... ዕፀ ጳጦስ ዘሲና..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የሙሴ ጽላት፣ በሲና ተራራ የታየችው ቁጥቋጦ (ዕፀ ጳጦስ) አንቺ ነሽ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ ጽላቱ የእግዚአብሔር ቃል እንዳለበት፣ አንቺም አካላዊ ቃልን ጸነስሽ። ዕፀ ጳጦስ በእሳት ሳይቃጠል እንደታየ፣ አንቺም መለኮትን ፀንሰሽ አልተቃጠልሽም።

​ምሥጢር፦ ድንግልናና እናትነት በአንድነት መኖራቸውን ያሳያል።
​ሐተታ፦ "በድንጋይ የተቀረጸ ቃል" በጽላት ይኖር ነበር፤ "በድንግል የተወለደ ቃል" ግን በሥጋ መጣ።
​ለኛ ያለው መልዕክት፦ የአምላክን ተአምራት በንጽሕና እንድናደንቅ።

​ለምሳሌ፦ ሰም በእሳት ሲነካ ይቀልጣል፣ እርሷ ግን መለኮትን (እሳትን) ታቅፋ አልቀለጠችም ይህ ዕፁብዕፁብ ያሰኛል
​ ዘጸአት ፫፥፪

​፲፩. "ጸናጽል ዘውስተ ልብሱ ለአሮን ካህን በትረ አሮን እንተ ሠረፀት..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የአሮን የልብሱ ጸናጽልና ያለ ውሀና ሳይተክሏት የበቀለችው በትር ነሽ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ የአሮን በትር ያለ ዘር እንዳበበች፣ አንቺም ያለ ሩካቤ ጸነስሽ።

​ምሥጢር፦ ድንግልናዋ ዘለዓለማዊ መሆኑን ያሳያል።
ዘኁልቁ ፲፯፥፰

​ "ሐውልተ ስምዕ ዘኢያሱ... ፀምር ዘጌዴዎን..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የኢያሱ የምስክር ሐውልት፣ የጌዴዎን ጸምር አንቺ ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ በጌዴዎን ጸምር ላይ ጠል እንደወረደ፣ በአንቺም ላይ መንፈስ ቅዱስ ወረደ።
​መሳፍንት ፮፥፴፯

​ "ሙዳየ ዕፍረት ወቀርነ ቅብዕ ዘሳሙኤል... ሥርው ዘዕሤይ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የሳሙኤል የሽቱ መያዣና የቀንድ ቅብዕ ነሽ፤ ዕሤይ የተመካባት ሥር አንቺ ነሽ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ የዳዊት አባት ዕሤይ ካንቺ በሚወለደው መሲሕ ተመካ።
​ ኢሳይያስ ፲፩፥፩
​
"ሠረገላተ አሚናዳብ... መሰንቆሁ ለዳዊት... አክሊሉ ለሰሎሞን..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የአሚናዳብ ሠረገላ፣ የዳዊት መሰንቆ፣ የሰሎሞን አክሊል ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ የታሸገች ገነት፣ የታተመች ምንጭ አንቺ ነሽ።
​ምሥጢር፦ ድንግልናዋ በዝግ የተጠበቀ መሆኑን ያሳያል።
​መኃልየ መኃልይ ፬፥፲፪

​ "መሶበ ወርቅ እንተ ኤልያስ... መስብክት ዘኤልሳዕ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የኤልያስ የወርቅ መሶብ፣ የኤልሳዕ መስበኪያ ነሽ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ በመሶብ መና እንደተጠበቀ፣ በአንቺም የሕይወት እንጀራ ተገኘ።
​ ዕብራውያን ፱፥፬

​"ዘኢሳይያስ ብኲርና... ዘዳንኤል... ደብረ ፋራን ዘዕንባቆም..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የኢሳይያስ ድንግል መውለድ፣ የዳንኤል ተራራ፣ የዕንባቆም የፋራን ተራራ ነሽ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ ድንጋይ ሳይፈነቀል ከተራራው እንደወረደ፣ ክርስቶስም ያለ ዘር ከአንቺ ተወለደ።
ኢሳይያስ ፯፥፲፬ ፣ ዳንኤል ፪፥፴፬

​"ምሥራቀ ዕፁት ዘሕዝቅኤል... ወሙፃአ ሕግ ዘቤተ ልሔም... ምድረ ኤፍራታ ዘሚክያስ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የሕዝቅኤል የተዘጋች ምሥራቅ፣ የሚክያስ የኤፍራታ ምድር ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ ጌታ ከገባባት በኋላ ተዘግታ የምትኖር ደጅ (ድንግልና) ነሽ።
​ማጣቀሻ፦ ሕዝቅኤል ፵፬፥፪

​ "ዕፀ ሕይወት ዘሶፎንያስ... ፈዋሲተ ቍስሉ ለናሆም... ትፍሥሕተ ዘካርያስ..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የሶፎንያስ የሕይወት ዛፍ፣ የናሆም የቁስል ፈዋሽ፣ የዘካርያስ ደስታ ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ በአዳም ላይ የመጣውን የኃጢአት ቁስል በአንቺ ልጅ ተፈወሰ።
​ ዘካርያስ ፱፥፱

​ "ሞገሶሙ ለሐዋርያት... እሞሙ ለሰማዕት... ወእኅቶሙ ለመላእክት..."
​አንቀጸ ንባብ፦ የሐዋርያት ሞገሳቸው፣ የሰማዕታት እናታቸው፣ የመላእክት እህታቸው ነሽ።

​አንቀጸ ትርጓሜ፦ ሐዋርያት በአንቺ ይበረታሉ፣ ሰማዕታት ፍቅርሽን አይተው ይታገሳሉ፣ መላእክት በንጽሕናሽ ይመሰላሉ።

​ምሥጢር፦ የቤተክርስቲያን ሁሉ እናት መሆኗን ይገልጻል።
​ለኛ ያለው መልዕክት፦ ድንግል ማርያም ለቅዱሳን ሁሉ የድል አክሊል መሆኗን ማወቅ።

​"ትምክሕቶሙ ለወራዙት ለደናግል ወመነኮሳት..."
​አንቀጸ ንባብ፦ ሌሊትና ቀን በደጆቿ ለሚተጉ መነኮሳት፣ ደናግልና ወጣቶች ትምክህታቸው አንቺ ነሽ።
​አንቀጸ ትርጓሜ፦ በንጽሕና ለሚኖሩ ሁሉ አርአያ ናት።
​መጠቅለያ (ግርምት)

​ኦ ድንግል ሆይ! ነቢያት በምሳሌ፣ ሐዋርያት በስብከት፣ መላእክት በውዳሴ ቢዘምሩልሽም፤ ገና "በማንና በምን አምሳል እንመስልሻለን?" እያልን እንገረማለን። አንቺ ከፍጥረት ሁሉ በላይ ነሽና!
​ለምሳሌ፦ ፀሐይን በሻማ ብርሃን መመሰል እንደማይቻል ሁሉ፣ ድንግልንም በፍጡር መመሰል አይቻልም። ነገር ግን ለፍቅሯ መግለጫ አባቶች እንዲህ ተቀኙላት።
​"ተፈሥሒ ፍሥሕት ሆይ" (ቅዱስ ኤፍሬም)።

ጸሎቷ በረከቷ ረድኤቷ አይለየን
​✍️​ ​“ለግሪክ ሰዎችና ላልተማሩም፥ ለጥበበኞችና ለማያስተውሉም ዕዳ አለብኝ፤”
በወንጌል አላፍርምና፤
አስቀድሞ ለአይሁዳዊ ደግሞም
ለግሪክ ሰው፥ ለሚያምኑ ሁሉ
የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን
ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎ እንደ ተጻፈ የእግዚአብሔር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና። ሮሜ 1÷14

እግዚአብሔር ሆይ የሚሳንህ ነገር የለምና የራቀውን አቅርበህ የረቀቀውን አጉልተህ እየሰማነው ካለነው መርዶና ሰቀቀን ዕረፍተ ሥጋንና ዕረፍተ ነፍስን አትንሣን

ጸልዩ በእንተ ሰላም
ስለ ሰላም እንጸልይ
ስለ ሀገራችን እንጸልይ
ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንጸልይ
በጭንቅ በመከራ ስላሉት እንጸልይ
በረሀብ በስደት ስላሉት እንጸልይ
በጽኑ ሕመም ተይዘው ስለሚሰቃዩት እንጸልይ
ስለ ሃይማኖት መሪዎች አባቶቻችን እንጸልይ
ስለ ሀገር መሪዎች እንጸልይ
የሰላም የምህረት የቸርነት ባለቤት እግዚአብሔር ሰላሙን ምህረቱን ቸርነቱን አይንሳን

አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ
ዘዝዋይ ገዳም
ሚያዝያ 21/8/2018 ✍️
⛪️⛪️⛪️⛪️⛪️⛪️⛪️

19/02/2026

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
የካቲት 13-በአባቱ በህርማኖስ ትእዛዝ ሰማዕትነትን የተቀበለው ታላቁ ሰማዕት የቅዱስ ፊቅጦር ልደቱ ነው፡፡
+ የሀገረ ሶርያው ሰማዕቱ ቅዱስ አውሳብዮስ ዕረፍቱ ነው፡፡ እርሱም ‹‹ሁለተኛው አውሳብዮስ›› የሚባለው ሲሆን መናኔ መንግሥት ወብዕሲት ነው፡፡ በሰማዕትነት ካረፈ በኋላ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ከሞት አስነሥተውት በሰማይ 14 ዓመት ተመልሶ ወደ ምድር መጥቶ 40 ዓመት የኖረ ሲሆን በተአምራቱና በትምህርቱ 85 ሺህ አረማውያንን አሳምኖ ያጠመቀ ነው፡፡
+ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት የከበረ ቅዱስ ሰርግዮስ ከእናትና ከአባቱ ከወንድሞቹም ጋር በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡

ሰማዕቱ ቅዱስ ሰርግዮስ፡- የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ አባቱ ቴዎድሮስና እናቱ ማርያም ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ እርሱንም የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ በሃይማኖት በምግባር አሳደጉት፡፡ ቅዱስ ሰርግዮስ 20 ዓመት ሲሆነው በጌታችን ስም ሰማዕት ይሆን ዘንድ ወደደ፡፡ በከሃዲውም መኮንን በቆጵርያኖስ ፊት ቀርቦ የጌታችንን እውነተኛ አምላክነት መሰከረ፡፡ መኮንኑም ይዞ ጽኑ ሥቃይን ካሠቃየው በኋላ አሠረው፡፡ በእስር ቤትም ሳለ ጌታችን የቅዱስ ሰርግዮስን ነፍስ ወደ ሰማይ አምጥቀው የቅዱሳን ሰማዕታትን መኖሪያ ያሳዩአት ዘንድ መላእክቱን አዘዛቸው፡፡ የቅዱስ ሰርግዮስ ነፍስ የዘላለም መኖሪያዋን አይታ ተጽናናች፡፡ በሥጋውም ከሕማሙና ከቁስሉ ሁሉ ተፈወሰ፡፡
ቀሲስ አባ መጹን እና ሁለት ዲያቆናት የቅዱስ ሰርግዮስን ተጋድሎ በሰሙ ጊዜ ተነሥተው ወደ ከሃዲው የአትሪብ ገዥ በመሄድ በጌታችን ታመኑ፡፡ መኮንኑም ሕዝቡ በተሰበሰበበት የጸና ግርፋትን ገረፋቸው፡፡ ሕዝቡም ስለቄሱና አብረውት ስላሉት ሰማዕታት ሲያዝኑ ዞሮ ገሠጻቸውና በሃይማኖት ጸንተው መኖር እንዳለባቸው ነገራቸው፡፡ በውኃም ላይ ጸሎት አደረገና በሕዝቡ ላይ በረጨ ጊዜ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀበሉ፡፡ ከዚያም የጌታችን አምላክነት በመመስከር ጮኹ፡፡ መኮንኑም እጅግ ተናዶ ራስ ራሶቻቸውን በሰይፍ አስቆረጣቸውና የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጁ፡፡ ቄሱን ግን ይዞ ከውሽባ ቤት የእሳት ማንደጃ ውስጥ ጨመረው፡፡ የታዘዘ መልአክም መጥቶ በጌታችን ስም 3 ጊዜ ምስክር እንደሚሆን ነግሮት ከእሳት አወጣው፡፡ መኮንኑም ቄሱን ወደ እስክንድርያ ልኮት ቄሱ ምስክርነቱን በዚያ ፈጽሞ የድል አክሊልን ተቀዳጀ፡፡
ከዚህም በኋላ መኮንኑ ቆጵርያኖስ የከበረ ቅዱስ ሰርግዮስን ከእስር አውጥቶ እጅግ አሠቃየው፡፡ የነሐስ መንኮራኩሮችን አምጥተው ከውስጣቸው አስገብተው አበራዩት፤ ሕዋሳቱም 4 ክፍል ሆኖ ሥጋው ሁሉ ተቆራረጠ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ፈወሰውና ያለ ምንም ጉዳት ጤነኛ አድርጎ አስነሣው፡፡ ዳግመኛም እንዲሰግድለት ጣዖትን አመጡ፡፡ ቅዱስ ሰርግዮስ ግን ጣዖቱን ቢረግጠው ከመሬት ወድቆ ደቀቀ፡፡ ‹‹አምላኬ›› ብሎ ያመልከው የነበረው መኮንኑ ቆጵርያኖስ ይህንን ሲያይ በመገረም ‹‹አምላክ ቢሆንስ ራሱን እንኳን ባዳነ ነበር ከእንግዲህስ በሰርግዮስ አምላክ አምኛለሁ›› ብሎ መሰከረ፡፡
ከዚህም በኋላ የንጉሡ የጭፍሮች አለቃ የከበረ ቅዱስ ሰርግዮስን ፈልጎ ያዘውና ቆዳውን ገፎ በተቀቀለ ኮምጣጤና ጨው ቁስሉን በማሸት በእጅጉ አሠቃየው፡፡ ነገር ግን ጌታችን መከራውን ያስታግስለትና ያጸናው ነበር፡፡ የቅዱስ ሰርግዮስን ተጋድሎ ሰምተው እናቱና እኅቱም ወደ እርሱ መጥተው ባዩት ጊዜ አለቀሱ፡፡ ከኀዘንም ብዛት እኅቱ ነፍሷ አለፈች፡፡ እናቱም ወደ ጌታችን በጸለየች ጊዜ ድና በሕይወት ተነሣች፡፡ በዚያንም ወቅት የሰማዕታትን ገድል የሚጽፍ የከበረ ዮልዮስ መጣ የቅዱስ ሰርግዮስን ገደል ከራሱ ተረዳ፡፡ ስለ ሥጋውም እንደሚያስብ ቃል ገባለት፡፡ ከዚህም በኋላ የከበረ ቅዱስ ሰርግዮስን በመንኮራኩር ውስጥ አሠቃዩት፡፡ በጆሮቹም የእሳት መብራቶችን ጨመሩበት፣ የእጆቹንና የእግሮቹን ጥፍሮች በጉጠት ነቀሏቸው፡፡ በአንገቱም ከባድ ድንጋይ አንጠልጥለው ከብረት አልጋ ላይ አስተኝተው ከታች እሳት አነደዱበት፡፡ በዚህም ወቅት ጌታችን ከመከራው አስታግሶ ጤነኛ አድርጎ አስነሣው፡፡ ይህንንም ያዩ ብዙዎች በጌታችን አመኑ፡፡ የጭፍሮቹም አለቃ ቅዱስ ሰርግዮስን ማሠቃየት በሰለቸው ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ቅዱስ ሰርግዮስም ይህንን ሲሰማ እጅግ ደስ ተሰኘ፡፡ አባቱና እናቱ ወንድሞቹም ከሀገሩ ሰዎች ጋር ሆነው ሊሰናበቱት መጡ፡፡ አፉን በልጓም ለጉመው ወደሚሰየፍበት ቦታ ሲወስዱት ደረሱ፡፡ እነርሱም የንጉሡን ጣዖታት ረገሙ፡፡ የጭፍሮቹም አለቃ የቅዱስ ሰርግዮስ ቤተሰቦችን ከእርሱ ጋር አብረው እንዲሰየፉ አዘዘና ሁሉም ተሰይፈው በመንግሥተ ሰማያት የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጁ፡፡
በሰማዕትነታቸውም ወቅት እንዲህ ሆነ፡- ከሕዝቡ ውስጥ አንድ ታናሽ ሕፃን እግዚአብሔር ዐይኖቹን ገልጦለት የቅዱሳን ሰማዕታትን ነፍሶቻቸውን መላእክት ወደ ሰማያት ሲያወጧቸው አይቶ ‹‹ጌታዬ አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ!›› እያለ በከፍተኛ ቃል ጮኸ፡፡ እናትና አባቱም የጭፍሮቹ አለቃ የሕፃኑን ድምጽ ሰምቶ እንዳያጠፋቸው አፉን አፈኑት፡፡ ነገር ግን ሕፃኑ በላዩ እስከተኙበትና ነፍሱን እስካሳለፈ ድረስ በመስከር መጮኹን አላቆመም ነበር፡፡ ከሰማዕታቱም ጋራ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን!
+ + +
ሰማዕቱ ቅዱስ አውሳብዮስ ዘሀገረ ሶርያ፡- ይኽም ቅዱስ የሶርያው መስፍን ልጅ ነው፡፡ ወላጆቹ በተግሣጽና በጥበብ ካሳደጉት በኋላ የሮሜውን ንጉሥ ልጅ በታላቅ ክብር አጋቡት፡፡ በሠርጉም ዕለት መንፈስ ቅዱስን የተመላች ቅድስት ወደሆነችው እኅቱ ወደ አውሎፊያ ዘንድ ገብቶ ‹‹እስቲ ምከሪኝ ልቤ ይህን ጋብቻ አይሻውም ዓለምን ንቆ መተውን እንጂ›› አላት፡፡ እኅቱም ‹‹የዚህ የኃላፊው ዓለም ጣዕም ምን ይጠቅምሃል? እንደ ሊቀጳጳሳት ድሜጥሮስ በድንግልና መኖር ይሻልሃል›› አለችው፡፡ ምሽትም በሆነ ጊዜ ወደ ሙሽራይቱ ጫጉላ ቤት ገብቶ የእነርሱ ውበትና ደምግባት እንደሚጠፋ ከዚህም ይበልጥ የሚጠቅማቸውን የጽድቅ ሥራ በመሥራት ድንግልናቸውን መጠበቅ እንዳለባቸው ሙሽራይቱን አዋያት፡፡ ሙሽራይቱም በሀሳቡ ተስማምታ ድንግልናቸውን በመጠበቅ በጾም በጸሎት እየዋሉ ሌሊትም ከባሕር ውስጥ ገብተው ቆመው ሲጸልዩ ያድሩ ጀመር፡፡ አትራ ወደምትባል ቤተ ክርስቲያን ሄደው አራት እልፍ ይሰግዳሉ፡፡
በአንዲት ዕለት የሶርያው ንጉሥ ሚስት ቅዱስ አውሳብዮስን አይታው እጅግ ወደደችው፡፡ ከባሮቿም ውስጥ ሁለቱን ልካ ካስመጣችው በኋላ በወርቅ አጊጣ በሐር በተነጠፈ አልጋ ላይ ሆና ጠበቀችው፡፡ ከእርሷም ጋር እንዲተኛ ስትጠይቀው ‹‹እኔስ ሚስቴንም እንኳን በግብር ያላወኩ ነኝና ተይኝ ንጉሡ ባልሽ በቤት ባይኖር ሰውም ባያየን እግዚአብሔር ግን ያየናልና እንዴት በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአት እሠራለሁ?›› በማለት ትቷት ሊወጣ ሲል ልብሱን ያዘችው፡፡ እርሱም ሮጦ በማምለጥ ቤተ ክርስቲያን ሲገባ እርሷ ግን በመጮህ ባሮቿ ሲመጡላት ‹‹ክፉ ነገርን አድርጎብኝ ሄደ›› ብላ በሐሰት ተናገረች፡፡ ጭፍሮቿም ቅዱስ አውሳብዮስን ከቤተ ክርስቲያን አውጥተው እየደበደቡ ወደ ንግሥቲቱ አመጡት፡፡ እጆቹንና እግሮቹንም አሥረው ከከተማ ውጭ በአራት ዕንጨቶች ላይ አሰቀለችው፡፡ ከባሮቿም ውስጥ አንዲቱ በንግሥቲቱ ተልካ ሄዳ አውሳብዮስን ‹‹ከተሰቀልክበት እንድታወርድህ ለእመቤቴ ያለችህን እሺ በላት›› አለችው፡፡ እርሱም ‹‹የአመንዝራን ቃል አልሰማም›› አላት፡፡ ንግሥቲቱም እሺ እንዳላላት ስታውቅ አንገቱን በገመድ አሳንቃ 160 ፍላጻዎችን በሰውነቱ ውስጥ እንዲጭምሩበት አደረገች፡፡ ጌታችንም ቅዱስ ሚካኤልንና ቅዱስ ገብርኤልን ልኮለት ፍላጻዎቹን ከሰውነቱ ውስጥ አወጡለትና ፍጹም ጤነኛ ሆነ፡፡
ንጉሡም ከሄደበት ሲመለስ ንግሥት ሚስቱን አውሳብዮስን ለስቅላትና ለሞት ያበቃችው በምን ምክንያት እንደሆነ ሲጠይቃት ‹‹አንተ በሌለህበት ወደ መኝታ ቤቴ ገብቶ ሊናገሩት የማይገባ ነገር ጠየቀኝ በከለከልኩትም ጊዜ በሥራዩ አሳመመኝ›› አለችው፡፡ ንጉሡም ተቆጥቶ ቅዱስ አውሳብዮስን ከተሰቀለበት አስወርዶ ካስመጣው በኋላ ለምን ይህን እንዳደረገ ጠየቀው፡፡ አውሳብዮስም እውነቱን በነገረው ጊዜ ጭፍሮቹን ምስክር ይሆኑ ዘንድ ሲጠይቃቸው ንግሥቲቱ ስትጮህ ወደ ውስጥ ሲገቡ ያጋጠማቸውን መሰከሩ፡፡ ንጉሡም የሚስቱን ነገር አምኖ በመቀበል በንዴት የቅዱስ አውሳብዮስን ሰውነቱን በሰይፍ አስቆርጦ ሥጋውን እንደ ላም ሥጋ ቆራርጦ በምንቸት አድርጎ በእሳት እንዲበስል አደረገው፡፡ ነገር ግን አሁንም ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ከምንቸቱ አውጥተው ከሞትም አድነው በማስነሣት ፍጹም ጤነኛ አደርገው አቆሙት፡፡

ከሞት ከተነሣም በኋላ በሀገሩ ውስጥ ሲሄድ ሰዎች አይተውት ለንጉሡ ስለነገሩት ንጉሡ ድጋሚ ካስመጣው በኋላ አራት ዛንጅሮች በአካላቶቹ ውስጥ በማስገባት እጅና እግሩን አሳስሮ በእሳት ውስጥ ጨመረው፡፡ የከበሩ ሁለቱ ቅዱሳን መላእክት አሁንም መጥተው ፈወሱት፡፡ መልአኩ ቅዱስ ዑራኤልም ነጥቆ ወደ ሰማይ አሳርጎት በዚያው በሰማይ 14 ዓመት ኖረ፡፡ ከዚያም ወደ ምድር ተመልሶ መጥቶ ወንጌልን እያስተማረ 40 ዓመት ኖረ፡፡ በእርሱም ትምህርት 85 ሺህ አረማውያን አምነው ተጠምቀዋል፡፡ ቅዱስ አውሳብዮስ በመጨረሻ ሰማዕትነቱንና ተጋድሎውን ፈጽሞ የካቲት 13 ቀን በክብር ዐርፏል፡፡ መታሰቢያውንም ለሚያደርግ እስከ ሰባት ትውልድ እንደሚምርለት ጌታችን ቃልኪዳን ገብቶለታል፡፡ የሰማዕቱ የቅዱስ አውሳብዮስ ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን!
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት በአባቱ በህርማኖስ ትእዛዝ ሰማዕትነትን የተቀበለው ታላቁ ሰማዕት የቅዱስ ፊቅጦር ልደቱ ነው፡፡ (የዕረፍቱን ዕለት ሚያዝያ ሃያ ሰባትን ይመለከቷል)
የከሃዲው ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስ ባለሟል በነበረው በገዛ አባቱ እጅግ ተሠቃይቶ ምስክርነቱን የፈጸመው ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ፊቅጦር ልደቱ ነው፡፡ ኅርማኖስ የተባለው ወላጅ አባቱ የክርስቲያኖችን ደም እንደ ውኃ ያፈስ የነበረው የዲዮቅልጥያኖስ ልዩ አማካሪና የሠራዊቱ አለቃ ነበር፡፡ እናቱ ማርታ ግን በክርስቶስ አምና የተጠመቀች ክርስቲያን ነበረች፡፡ እንዲያውም ልጇን ቅዱስ ፊቅጦርን ከመውለዷ በፊት የአምላክ እናት የቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ወዳለበት ሄዳ ‹‹እመቤቴ ማርያም ለኢየሱስ ክርስቶስ ደስ የሚያሰኘውን ልጅ ስጪኝ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስን ደስ የማያሰኝ ልጅ ከሆነ ግን ማኅፀኔን ዝጊልኝ›› ብላ በጸለየችው ጸሎት ነው ቅዱስ ፊቅጦርን ያገኘችው፡፡
ሰማዕቱ ቅዱስ ፊቅጦር በዓለም ላይ ያሉ በክርስቶስ ያመኑ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ በግፍ ያስገድል በነበረበት ወቅት የተገኘ ታላቅ ሰማዕት ነው፡፡ ፊቅጦርን ገና 15 ዓመት እንደሆነው ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ ‹‹ከፍ ባለ ስልጣን አስቀምጥሃለሁ፣ እጅግ ብዙ ወርቅና ንብረትም እሰጥሃለሁ፣ በእስክንድርያም ላይ ገዥ አድርጌ እሾምሃለሁ ክርስቶስን ማመንህን ተውና ወደ ቤተ መንግሥቴ ግባ›› ቢለውም ቅዱስ ፊቅጦር ግን ብዙ መከራንና ሥቃይን ተቀብሎ ሰማዕት መሆንን መረጠ፡፡ ቅዱስ ፊቅጦርም ዲዮቅልጥያኖስን ‹‹ክርስቶስን በምታፈቅረው ጊዜ አፈቀርኩህ ወደ አንተም መጣሁ፤ ክርስቶስን በጠላኸው ጊዜ ግን እኔም ጠላሁህ፣ ቤትህንም ጠላሁ›› ብሎታል፡፡
ከብዙ ጊዜም በኋላ ዲዮቅልጥያኖስ ቅዱስ ፊቅጦርን በመንግሥቱ ውስጥ ሦስተኛ ማዕረግ አድርጎ ሾመው፡፡ እርሱ ግን ይጾማል ይጸልያል እንጂ በንጉሡ ቤት አይበላ አይጠጣም ነበር፡፡ ዕድሜውም 27 ብቻ ነበር፡፡ አባቱንም ከጣዖት አምላኪነቱ እንዲመለስ ቢመክረው ሄዶ ለንጉሡ ከሰሰው፡፡ ፊቅጦርም ‹‹ለአንተ ለጣዖት አምላኩ አገልጋይ አልሆንም›› በማለት በንጉሡ ፊት ትጥቁን ፈቶ ጣለ፡፡ የቅዱስ ፊቅጦር ወላጅ አባቱ ኅርማኖስ የከሃዲው ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስ የቅርብ እንደራሴና መስፍን ስለነበር ልጁ ፊቅጦርን የንጉሡን ሹመትና ልመና እንዲቀበል ብዙ ሲያግባባው ነበር፡፡ አባቱም ልጁ በሀሳቡ እንዳልተስማማለት ሲያውቅ ከዲዮቅልጥያኖስ ጋር ተማክሮ ልጁን ቅዱስ ፊቅጦርን ወደ እስክንድርያና ወደ ተለያዩ ሀገሮች በግዞት ተልኮ በዚያም ተሠቃይቶ እንዲሞት ፈረደበት፡፡

ወደ ግብፅም ልከው በዚያ እጅግ አሠቃዩት፡፡ መልአክም ነጥቆ ወስዶ በሰማያት የሰማዕታትን ክብር አሳይቶት ወደ ምድር መለሰው፡፡ ክፉዎቹም በብረት አልጋ አስተኝተው ከሥሩ እሳት አነደደዱበት፡፡ በሌላም ልዩ ልዩ በሆኑ ማሠቃያዎች እጅግ አሠቃዩት፡፡ መልአክም ተገልጦ ፈወሰው፡፡ ወደ እንዴናም አጋዙትና በዚያም ብዙ አሠቃዩት፡፡ ምላሱን ቆረጡት፤ በችንካርም ጎኖቹን በሱት፤ ቁልቁል ሰቅለውም ቸነከሩት፤ በእሳትም ውስጥም ጨመሩት፤ ዐይኖቹን አወጡት፤ እሬትና መራራ ሐሞትንም አጠጡት፡፡ ደግመውም ዘቅዝቀው ሰቀሉት፡፡ ጌታችንም ተገልጦ ካጽናናው በኋላ ፈወሰውና ፍጹም ጤነኛ አደረገው፡፡ ፊቅጦር፣ ፋሲለደስ፣ ቴዎድሮስ በናድልዮስ፣ አውሳብዮስና መቃርዮስ እነዚህ ሰማዕታት በአንድነት በአንድ ዘመን አብረው ኖረው ተሰውተው ሰማዕት የሆኑ የሥጋም ዝምድና ያላቸው የነገሥታት ልጆች ናቸው፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም የቅዱስ ፊቅጦርን ዐይኑን አስወለቀው፣ ነገር ግን የታዘዘ መልአክ መጥቶ የዓይኑን ብርሃን መልሶለታል፡፡ ሰማዕቱ በመዝለል ባሕር የሚሻገር እንደ አሞራ የሚመስል ፈረስ ነበረው፡፡ ከዚህም በኋላ ማሠቃየቱ ቢሰለቻቸው ሚያዝያ 27 ቀን አንገቱን ሰይፈው በሰማዕትነት እንዲያርፍ አድርገውታል፡፡
ሰማዕቱ ቅዱስ ፊቅጦር አንድ የሚነገር ትልቅ ታሪክ አለው፡፡ እርሱም በሰማዕትነት ካረፈ ከብዙ ዘመን በኋላ በራእይ ተገልጦ በ8ኛው ሺህ ዘመን በሀገራችን በኢትዮጵያና በግብፅ እንዲሁም በቁስጥንጥንያና በሮም ወደፊት የሚሆነውን ነገር ሁሉ በግልጽ የተናገረ መሆኑ ነው፡፡ ‹‹ስለ ሃይማኖት ቅዱስ ፊቅጦር ያየው ራእይ›› የሚል መጠሪያ ያለው ይህ ራእይ በሀገራችን ጎጃም ደብረ ጽሞና ገዳም ውስጥ ይገኛል፡፡ ይህንን በተመለከተ ቅዱስ ፊቅጦር የተናገረውንና ቅዱስ ገድሉ ላይ የተጻፈውን ቀጥሎ እንመለከተዋለን፡-
‹‹…በእስላሞችም ጊዜ በግብፅ ሀገር ሁሉ የክርስቶስ ሕግ አይቋረጥም፡፡ የጾም፣ የጸሎትና የቍርባን እምነት ይኖራል፡፡ ከእስላሞች ጋር እየኖሩ የሃይማኖት ጽናት ትበዛለች፤ በማርቆስ መንበርም የሊቀ ጳጳሳት መሾምም አይቋረጥም፤ በሊቀ ጳጳሳት እጅ በየደረጃው የጳጳሳት፣ የኤጲስ ቆጶሳት፣ የቀሳውስትና የዲያቆናት ሹመትም አይቋረጥም፡፡ የእስላሞችም መንግሥት ጥቂት ዘመናት ናቸው፡፡ ከጥቂት ዘመናት በኋላ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ ሀገር ክርስቶስን የሚወድ ቅዱስ ሰው ያነግሣል፡፡ ዐረማውያንም በእርሱ እጅ ይደመሰሳሉ፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ግብፅ ሀገር ሄዶ እስላሞችንና መንግሥታቸውን ሁሉ ያጠፋል፡፡ እግዚአብሔር በቍስጥንጥንያ እርሱን የሚወድ ስሙ ትውልደ አንበሳ የተባለ ሰው ያነግሳል፡፡ ከኢትዮጵያ ንጉሥ ጋር ይገናኝ ዘንድ ይመጣል፡፡ በግብፅ መሀል ቦታ ላይ ይገናኛሉ፡፡ ከእርሱ ጋርም የእስክንድሪያ ሊቀ ጳጳሳትና የቍስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት ይገናኛሉ፡፡ የኢትዮጵያ ንጉሥ ሠራዊቱን በደቡብ በኩል ትቶ የቍስጥንጥንያም ንጉሥ ሠራዊቱን በሰሜን በኩል ትቶ ሁለቱ ነገሥታትና ሁለቱ ሊቃነ ጳጳሳት ተገናኝተው እርስ በእርሳቸው ሰላምታ ይሰጣጣሉ፤ ሊቃነ ጳጳሳቶቹ በመንበራቸው ላይ ተቀምጠው ነገሥታቱን ‹በየመንበራችሁ ላይ ተቀመጡ› ይሏቸዋል፡፡ የቍስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት ‹የእኛ ሃይማኖት ትበልጣለች› ይላል፡፡ የእስክንድሪያውም ሊቀ ጳጳሳት ‹እግዚአብሔር የሰጠኝን ቃል እኔ እነግራችኋለሁ› ይላል፡፡ ሁለቱ ነገሥታትም ‹አባታችን በል ንገረን› ይሉታል፡፡ ‹የአባ ሲኖዳ ወደምትሆን ወደዚህች ታላቅ ቤተክርስቲያን ገብተን በአንዲት ታቦት ላይ እኔ እቀድሳለሁ፣ ይህ ባልደረባዬ ሊቀ ጳጳሳት በአንዲቷ ታቦት ላይ ይቀድስ፤ ሁሉም ሕዝብ ሠራዊቶቻችሁም መጥተው ይመልከቱ› ይላል፡፡ ‹መንፈስ ቅዱስ እያያችሁት ከሁለታችን በአንዱ ቁርባን ላይ ከወረደ በዚያ ሃይማኖት ሁላችን እንሂድ፣ ሃይማኖቷም ትታወቃለች ቀንታለችና› ይላቸዋል፡፡ ሁለቱ ነገሥታት ‹እሺ በዚህ ቃል ተስማምተናል፣ የእግዚአብሔር ምክር ናትና› ይሉታል፡፡ ያን ጊዜ ሁለቱ ነገሥታትና ሊቃነ ጳጳሳት ሠራዊቶቻቸውም ሁሉ ካህናቶቻቸውም፣ ሕዝቡም ወደዚህች ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ይገባሉ፡፡ ሁለቱ ሊቃነ ጳጳሳትም በሁለቱ ታቦታት ላይ ይቀድሳሉ፡፡ በዚያ ያሉ ሁሉ እያዩ መንፈስ ቅዱስ በነጭ ርግብ አምሳል ከብርሃን ጋር የእስክንድሪያው ሊቀ ጳጳሳት በቀደሰው ቍርባን ላይ ይወርዳል፡፡ ያን ጊዜ የኢትዮጵያ ንጉሥ ይደሰታል፣ የእርሱም ሊቀ ጳጳሳት ነውና፡፡ በእግዚአብሔር ፊትም የእርሱ የሃይማኖት ሕግ የተወደደ ይሆናል፡፡ የሮም ንጉሥ ግን ከሕዝቦቹ ጋራ ያዝናል፡፡ መጻሕፍቶቻቸውን ሁሉ ሰብስበው ወደ ባሕር ይወረውሯቸዋል፡፡ ሃይማኖታቸውንም ስለአጠፋና መናፍ*ቃን ስላደረጋቸው የቀድሞውን ሊቀ ጳጳሳቸውን ሊዎንን ይረግሙታል፡፡ ሁሉም ወደ አንዲት የእስክንድሪያ ሊቀ ጳጳሳትና የኢትዮጵያ ንጉሥ ሃይማኖት ይመለሳሉ፡፡ ሮምም፣ ግብፅም፣ ኢትዮጵያም ሁሉም የተስማሙ ይሆናሉ፤ በመካከላቸውም ጽኑ ፍቅር ይሆናል፡፡ ሁሉም ሃሌ ሉያ እያሉ እግዚአብሔርን ፈጽመው ያመሰግኑታል፡፡ የኢትዮጵያ ንጉሥና የሮም ንጉሥ እርስ በእርሳቸው እጅ መንሻንና ሰላምታን ተሰጣጥተው ወደየሀገራቸው ይመለሳሉ፡፡ ቅዱስ ፊቅጦርም ለእናቱ የሚነግራትን ይህንን ሁሉ ትንቢት ከጨረሰ በኋላ ‹እናቴ ማርታ ሆይ ሰላም ላንቺ ይሁን› ብሎ ከእርሷ ተሰወረ፡፡›› የሰማዕት የቅዱስ ፊቅጦር ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን!
ከገድላት አንደበት
✞ ✞ ✞

15/02/2026

#ዘወረደ
(የዐቢይ ጾም የመጀመሪያው ሳምንት )

የዐቢይ ጾም የመጀመሪያው ሳምንት ዘወረደ ይባላል፡፡

‹‹ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ›› የሚልና ይህንን የመሳሰለ ጌታ እኛን ለማዳንና ፍቅሩን ሊገልጽልን ከሰማያት መውረዱን ከድንግል ማርያም የእኛን ሥጋ መዋሐዱን የሚያዘክር ምስጋና የሚቀርብበት ሳምንት ነው፡፡ ሌላም ስም አለው ይባላል፡፡ ይህ ጾም የጾም መግቢያ የመጀመሪያ ሳምንት የምንጾመው ጾም ሲሆን #ሕርቃል የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡

?
?
በ614 ዓ.ም ኪርዮስ የተባለ የፋርስ ንጉሥ ኢየሩሳሌምን በመውረር ጥቃት አደረሰ፡፡ በዚህ ወቅት በኢየሩሳሌም ንግሥት ዕሌኒ በሠራችው ቤተመቅደስ ውስጥ ሲገባ ንግሥቷ በክብር አስቀምጣው የነበረው የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል እንደ ፀሐይ ሲያበራ አገኘው፡፡ ቢነካው አቃጠለው ዲያቆናቱን አሸክሞ ሌላውን ንዋየ ቅድሳት ዘርፎ 60 ሺህ የሚደርሱትን አቁስሎ ገድሎ 3 ሺህ የሚሆኑትን ማርኮ ከተማዋንም ቃጥሎ ወደ ፋርስ ባቢሎን ይመለሳል፡፡ በዚህ ጊዜ ከጦርነቱ ያመለጡ በየዋሻው በየጉራንጉሩ ገብተው የተሸሸጉ ተሰብስበው ከ14 ዓመት በኋላ በ628 ጩኸታቸውንና የደረሰባቸውን በደል ለክርስቲያኑ የሮም ንጉሥ ሕርቃል ይነግሩታል። እርሱም ሐዋርያት ሰውን የገ*ደ*ለ እድሜውን በሙሉ ይጹም ስላሉ እንዴት ላድርገው አላቸው እኛ የአንተን እድሜ ተከፋፍለን እንጾማለን ብለው አንድ አንድ ሳምንት ደርሷቸው ጾሙን በሚገባ ጾመውታል፡፡

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልና የተማረኩ ክርስቲያኖችን ለመመለስ ሕርቃል ጦር መዝዞ በኪርዮስ ላይ ተነሳበት ድል ለሕርቃል ሆነና መስቀሉን ያለበትን አጥቶ ሲቸገር መስቀሉን ሲቀብርና ዲያቆናቱን ሲያስገድል በመስኮት ሆና ያየችው ከኢየሩሳሌም የተማረከች አንዲት ብላቴና አሳይታው አውጥቶ በልብሰ መንግሥቱ ጠቅልሎ ወደ ቁስጥንጥንያ ተመለሰ፡፡ የተማረኩት በሙሉ ነጻ ወጡ ይህን ለማሰብ ለማስታወስ በተጨማሪ በኃጢአት ላይ ድል እንድናገኝ መንፈሳዊ ጦር በውስጣችን እንዲበዛልን መስቀልህ ከምርኮ እንደተመለሰ እኛንም ከኃጢአት ምርኮ መልሰን ለሕርቃል ድል መንሳትንና በጠላቶቹ ላይ ኃይልን እንደሰጠኸው ለእኛም በኃጢአት ላይ ድል መንሳት መንፈሳዊ ኃይልን ስጠን እያልን እንጾመዋለን፡፡

በጌታ ጾም ላይ እንዲጾም የሆነበት ምክንያት ጾሙ የጌታ ጾም በሚጾምበት ወቅት ላይ ስለተጾመ ቤተክርስቲያናችን አብራ ደንግጋዋለች፡፡ እዚህ ላይ በዚያን ጊዜ ለሕርቃል ሕዝቡ ሱባኤ ይዞለታል፡፡ ዛሬም እኛ ለቤተክርስቲያን ያደረግነውን በማሰብ እግዚአብሔር አምላክ ለሕርቃል የሰጠውን በጠላቶቹ ላይ ድል መንሳትን ለእኛም እንዲሰጠን የምንጠይቅበት ስለሆነ የመጀመሪያውን ሳምንት በሕርቃል ሰይመን ጾሙን እንጾማለን፡፡ የእኛ ጠላት የጨለማ ገዥ የሆነው ዲያቢሎስ ነውና እሱን ደግሞ በጾም እንደምናሸንፈው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮናል፡፡

« #ዘወረደ» ማለትም በቀጥታ፣ ቃል በቃል ሲተረጐም « #የወረደ» ማለት ነው፡፡ ይህም በምስጢሩ አምላክ ወልደ አምላክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም በቅዱስ ፈቃዱ ሰው ሆኖ ከሰማየ ሰማያት፣ ከባሕርይ ልዕልናው በትሕትና ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱን የሚያመላክት፣ ይህም የሚታወስበት፣ የሚወሳበት የዐቢይ ጾም አንደኛው ሳምንት ነው፡፡ ዮሐ.3፥13፡፡

ሳምንቱ #ሙሴኒ ይባላል። ይህ የተባለበትም ምክንያት በዚሁ ሳምንት መጀመሪያ የሰኞ ዕዝል «ከመዝ ይቤ ሙሴ ፀዓቱ እምትእይንት» «ሙሴ ከከተማ መውጣቱ እንደዚህ ነው አለ» ስለሚል እንደዚሁም የዚሁ ዕለት ማለት የሰኞ አቡን «ሙሴኒ ይቤ በውስተ ኦሪት ምድር ሰናይት» እያለ የሙሴን ታሪክ ስለሚያጠቃቅስ ሳምንቱ ሙሴኒ ተባለ፡፡ ነቢያትም አርባ አርባ ቀን ጾመው ከአለፉ በኋላ የሙሴ ሕግና ትንቢተ ነቢያት ፈጻሚ የሆነው ምላካችን እንደ እነሱ 40 ቀንና 40 ሌሊት መጾሙን የሚያስታውስ ነው፡፡ /ዘፀ.24፥18፤ 1ኛ.ነገ.19፥8፤ ማቴ. 4፥1-4/፡፡

25/01/2026

የዘመኑ ትዳርና የጥቅም ድራማ⁉️
••••••••••••••••••••••••••••

ድሮ ትዳር “ቅዱስ” እና የነፍስ ውህደት ነበር ። አሁን ግን ትዳር “ንግድ ኢንቨስትመንት” (Investment) ሆኗል። ሴቷ የባንክ ደብተር ታያለች፤ ወንዱ የመልክ ማራኪነት ይለካል። ፍቅር? እሱማ ድሮ በነ አያቶቻችን ዘመን ቀረ ! ዛሬ ጥቅም ባለበት ፍቅር አለ፤ ጥቅም ሲያልቅ ግን ፍቺው ቀዳሚ ይሆናል ።

የጥሎሽ ገበያና የ6 ወር ትዳር 💰

ሰርግ ሲታሰብ የሚወራው ስለ ፍቅር ሳይሆን ስለ ወጪ ነው። ወጣቱ ገና ትዳር ሳያስብ የሰርጉ ወጪና የሆቴሉ ድግስ ያስጨንቀዋል። ለአንድ ቀን ጭብጨባና ለሰዎች እይታ ተብሎ የሚገባ የ10 ዓመት ብድር መጨረሻው ኪሳራ ነው። የሚገርመው ያ ሁሉ ተደግሶና ተበልቶ፣ በስድስት ወር ውስጥ “አልተስማማንም” በሚል ሰበብ ይፋታሉ። ምክንያቱም ትዳሩ የተመሰረተው በፎቶና በቪዲዮ ላይ እንጂ በመግባባት ላይ አይደለም ።

የስፖንሰር ፍለጋና የመልክ ምርጫ 🏧

እህቴ ሆይ… እውነት እንነጋገር፤ ወንድን እንደ “ኤቲኤም” (ATM) ማየት መቼ ነው የምታቆሙት? “የምወደው ሰው ደሃ ነው” ብለሽ ትተሽው፣ የማትወጂውን ሀብታም ስታገቢ በገንዘብ የተገዛ ትዳር ገንዘቡ ሲያልቅ አብሮ እንደሚያልቅ አታውቂም? ወንዶችም ብትሆኑ ሴትን እንደ ዕቃ ወይም እንደ “የቤት ጌጥ” አትዩ። ውበት ይረግፋል፣ መልክ ይጠወልጋል፤ የሚቀረው ግን አብሮ አደግነትና መከባበር ብቻ ነው ።

የቲክቶክ ቪዲዮና የውሸት ጥንዶች 📱

አሁን አሁን መፋታት “ዘመናዊነት” እየሆነ መጥቷል ። ሶሻል ሚዲያ ላይ የምናያቸው “የውሸት ጥንዶች” (Couples) የትክክለኛውን ትዳር ትርጉም አበላሹት ። “እከሌ ሚስቱን ዱባይ ወሰዳት፣ አንተ ግን ሱሉልታ አልወሰድከኝም!” የሚል የፉክክር ኑሮ ቤትን ሲኦል ያደርገዋል ። ትዳር ማለት የታመመ መጠየቅ፣ የተራበ ማጉረስና የወደቀን ማንሳት እንጂ የቲክቶክ ትዕይንት አይደለም ።

የጭሰኛው የመጨረሻ መልእክት⚠️

ወጣቱ ሆይ… አትፍራ፤ ትዳር ከባድ ቢሆንም ጣፋጭ ነው። ግን ስታገባ ለሰው፣ ለገንዘብ ወይም ለመልክ ብለህ አታግባ ። ለፍቅርና ለመግባባት ብለህ አግባ ። ቤትህን በሲሚንቶ ሳይሆን በፍቅር ገንባው፤ ያኔ ንፋስ ቢመጣ አይፈርስም ።

የቲክቶክ “ገለባ” ሰለቸን እኮ፤ ቁም ነገር እናውራ !

ጭሱ ከኔ፣ እሳቱ ከአንተ! 🦁

📢 ይህ እውነት የህሊናህን በር ካንኳኳው፦
• ለእውነተኛ ፍቅርና ለትዳር ክብር ዋጋ ካለህ Like አድርግ።
• ትውልዱ ከጥቅም ትስስር እንዲወጣ Share በማድረግ እሳቱን አቀጣጥለው።
• ለተጨማሪ የህሊና ወጎችና የጭሰኛው ፍልስፍና ገጻችንን Follow ያድርጉ ።

11/01/2026

╭✥ ተግሣጸ ዮሐንስ አፈወርቅ ክፍል 5 ✥╮
🌷ተግሣጽ ፲፰
ክፉ ሰው በክፋቱ ሳለ የትሕትና ሥራ መሥራት አይቻለውም። ድህነት ሰውን እንዲገሠጽ እንዲመከር ያደርገዋል። ትሩፋት መሥራትና እግዚአብሔርን መፍራት ክብር ያሰጣል። መንግሥተ ሰማያትን እንወርስ ዘንድ ትዕቢትን መጣል ስስትን መተው ይገባናል።
🌷ተግሣጽ ፲፱
ክርስቶስን፣ ሐዋርያትን መምሰልን ከወደድን ጠላቶቻችንን እንወድ ዘንድ ይገባናል። ፍቅርን አጽንተን እንያዝ። እስመ ይእቲ ሥነ ትዕዛዛት። የሕግጋት ሁሉ ጌጥ ናትና። ፍቅር በባልንጀራ ላይ ክፉ አታሠራም። ስንኳን ማሠራት በባልንጀራ ላይ ክፉ ነገርን አታሳስብም። ለሰውነታችን በጎ በጎውን እንደምንሻላት ሁሉ ለባልንጀራችንም ይህንኑ መሻት ይገባናል። እርስ በእርሳችን አንድ መሆንን አንተው። በሰውነታችን ቂም እንደማንይዝ ሁሉ በባልንጀራችንም ቂም መያዝ አይገባንም። ሰውነታችንን እንደማንቆጣት፣ እንደማንበሳጭባት ሁሉ በሌላውም ሰው መበሳጨት አይገባም። ለሰውነታችን እንደምናዝንላት ለሌላውም እንዘንለት።
🌼ተግሣጽ ፳
መከራ፣ ጭንቅ የሚሆን ነገር በመጣብን ጊዜ ለበጎ ነገር እንዘጋጅ። በእግዚአብሔር ፊት ብናለቅስና ወደ እርሱ ብንቀርብ ረድኤቱን ይሰጠናል። ለእኛ ለክርስቲያኖች የሚጠቅመንንና የማይጠቅመንን ለይቶ ማወቅ አለብን። የሚመጣባችሁን መከራ በአኰቴት ተቀበሉ። የሚመጣባችሁን ብትታገሡ ንዑዳን ክቡራን ናችሁ። ኢዮብን አብነት አድርጉት። የመጣብንን መከራ ሁሉ ታግሠን ብንቀበል ዕጥፍ ዋጋን እናገኛለን።
🌼ተግሣጽ ፳፩
ትንሣኤ ሙታን አይቀርም። ቅድስት ቤተክርስቲያንን አጋንንት ድል አይነሷትም። ወዳጆቼ ሆይ እንጠበቅ ዘንድ ይገባናል። ከሞት በኋላ በወዲያኛው ዓለም ንስሓ ስለሌለ በዚህ ምድር ሳለን ንስሓ እንግባ። በወዲያኛው ዓለም የሚያዝኑት ኀዘን አይረባም አይጠቅምም። ነገር ብትሰማ በሆድህ እምሽክ ይበል እንጂ አትናገር። የባልንጀራችንን በደል መሠወር ይገባናል። ሰው ሆኖ ሰው ማማት፣ ሰው ሆኖ ሰው መንቀፍ አይገባም። በነገር ምክንያት የፈረሱ ብዙ ቤቶች አሉ። ብዙ ሰዎች በነገር ተጣልተዋል። እንዲህ ከሆነ ሌላውን እንዳናማ እንጠንቀቅ። ያሳዘነህ ሰው ቢኖር ለእግዚአብሔር ንገር። የሌላውን ሰው ኃጢአት ለሰው ብትናገር ትጎዳለህ እንጂ አትጠቀምምና።
💐ተግሣጽ ፳፪
እግዚአብሔር በእምነት በጸሎት ለሚሹት ሰዎች ዋጋቸውን እንደሚሰጣቸው እንደዚሁ በእምነት በጸሎት የማይሹትን ሰዎች ይፈርድባቸዋል። ቂም በቀልን ከእኛ እናርቅ። ድንቁርናን በዕውቀት እናርቅ። ኃጢአትን በንስሓ እናርቅ። ቃላችንን ለጸሎት እጃችንን ለምጽዋት ልናነሣ ይገባናል። ልቡናችሁን ሰማያዊ አድርጉ። በሰባቱ ጊዜያት መጸለይ ይገባናል። ሰውን ንጽሐ ልብ ከደረሰ በኋላ ዲያብሎስ ድል መንሣት አይቻለውም። ሰውነታችንን በፍጹም ትዕግሥት ልናጥረው ይገባናል። ሰይጣን ዓይናችንን እይ እይ በማለት፣ ልብን ተቆጣ ተቆጣ በማለት ይፈትነዋል። ይህን ጊዜ እንታገሥ። የአድማስ ደንጊያ ከሁሉ በላይ እንደሆነ መከራን የሚታገሡ ሰዎችም ከሁሉ በላይ ይሆናሉ። ሰይጣን ድል አይነሳቸውም። ባልንጀራህ ተቆጥቶ በጠላትነት ቢነሣብህ ተሠውረህ ፍግግ ፍግግ በል። ደግሞ ይስቅብኛል ብሎ እንዳያዝን ተሠውረህ ፍግግ ፍግግ በል። ብስጩ ሰው ከትንሽ ልጅ ያንሣል። የሚታገሥ ሰው ግን አእምሮው ፍጹም ነው።

ስብሐት ለ እግዚአብሔር !

02/01/2026

#ስለ ሴት ልጅ ጉዳይ መፅሃፍ ቅዱስ ምን ይላል?

1/1ኛ ቆሮንጦስ 14፡34 ላይ እንዲህ ይላል «ሴቶች በማህበር ዝም ይበሉ ህግ ደግሞ እንደሚል እንዲገዙ እንጂ እንዲናገሩ አልተፈቀደላቸውምና። ለሴት በማህበር መካከል መናገር ነውር ነውና ምንም ሊማሩ ቢዱወዱ በቤታቸው ባሎቻቸውን ይጠይቁ፡፡»ይላል

2/ሴት ግን በዝግታ ትኑር እንጂ ልታስተምር ወይም በወንድ ላይ ልትሰለጥን አልፈቅድም፡፡ (1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 2:12

3/ ነገር ግን የወንድ ሁሉ ራስ ክርስቶስ፥ የሴትም ራስ ወንድ፧ የክርስቶስም ራስ እግዚአብሔር እንደ ሆነ ልታውቁ እወዳለሁ፡፡ (1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፡3)

4/ ሚስትም ከባልዋ አትለያይ፧ ብትለያይ ግን ሳታገባ ትኑር ወይም ከባልዋ ትታረቅ።(1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 7፡10-11)

5/ ራስዋን ሳትሸፍን ግን የምትጸልይ ወደም ትንቢት የምትናገር ሴት ሁሉ ራስዋን ታዋርዳለች፤ እንደ ተላጨች ያህል አንድ ነውና፡፡ (1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፡5)

6/ ሚስቶች ሆይ፥ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤ (ወደ ኤፌሶን ሰዎች 5:22

7/ሚስቶች ሆይ፥ በጌታ እንደሚገባ ለባሎቻችሁ ተገዙ፡፡ (ወደ ቆላስይስ ሰዎች 3:18)

8/ሴት ግን በዝግታ ትኑር እንጂ ልታስተምር ወይም በወንድ ላይ ልትሰለጥን አልፈቅድም፡፡ አዳም ቀድሞ ተፈጥሮአልና፥ በኋላም ሔዋን ተፈጠረች፡፡ (1ኛ ወደ ጢሞቴዎ11፡12)

9/ የተታለለም አዳም አይደለም፧ ሴቲቱ ግን ተታልላ በመተላለፍ ወደቀች፤

ነገር ግን በእምነትና በፍቅር በቅድስናም ራሳቸውን እየገዙ ቢኖሩ በመውለድ ትድናለች፡፡ (1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 2፡14-15)

10/ወንድ የእግዚአብሔር ምሳሌና ክብር ስለ ሆነ ራሱን መከናነብ አይገባውም፤ ሴት ግን የወንድ ክብር ናት፡፡ ሴት ከወንድ ናት እንጂ ወንድ ከሴት አይዷለምና፡፡ ሴት ስለ ወንድ ተፈጠረች እንጂ ወንድ ስለ ሴት አልተፈጠረምና፡፡ ስለዚህ ሴት ከመላእከት የተነሣ በራስዋ ሥልጣን ሊኖራት ይገባል፡፡ (1ኛ ወዷ ቆሮንቶስ

ሰዎች 11፡7-10)::

+++ ነገረ ተዋህዶ +++ ================"አማኑኤል ዘበትርጓሜሁ እግዚአብሔር ምስሌነ " አማኑኤል ማለት "እግዚአብሔር ከሥጋችን ሥጋ ከነፍሳችን ነፍስ ነስቶ ከኛ ጋር ሆነ ÷ አምላ...
25/12/2025

+++ ነገረ ተዋህዶ +++
================
"አማኑኤል ዘበትርጓሜሁ እግዚአብሔር ምስሌነ " አማኑኤል ማለት "እግዚአብሔር ከሥጋችን ሥጋ ከነፍሳችን ነፍስ ነስቶ ከኛ ጋር ሆነ ÷ አምላክ ሰው ሆነ ሰው አምላክ ሆነ ማለት ነው ።"
"ኢመፍትው ከመ ንስምዮ ለ እግዚአብሔር ቃለ ክርስቶስ ዘእንበለ ትስብእት ወኢ ክርስቶስሃ ይሰመይ ትስብእት ዘእንበለ መለኮቱ "
መለኮቱን ከትስብእት ለይተን መለኮቱን ብቻ ክርስቶስ ልንል አይገባንም ÷ ትስብእትንም ከመለኮቱ ለይተን ትስብእቱን (ሰውነቱን ብቻ) ክርስቶስ ልንል አይገባም።
ክርስቶስ ማለት የመለኮትን ባሕርይ ገንዘብ ያደረገ የትስብእት እና የትስብእትን ባሕርይ ገንዘብ ያደረገ የመለኮት የተዋህዶ ስም ።
ክርስቶስ ማለት ከ ሁለት አካል አንድ አካል ÷
ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ የሆነ የአምላክ የተዋህዶ ስም ነው።

✍ አለበለዚያ መለኮቱን ከሰውነቱ ÷ ሰውነቱን ከመለኮቱ ለይተን መለኮቱን ብቻ ወይም ሰውነቱን ብቻ ክርስቶስ ካልን የአማኑኤልን ጌትነቱን ÷ አምላክነቱን ከባሕርይ አባቱ ከ አብ መለየት ይሆናል ።

✍ ሥጋን ከለበሰ በኋላም የእግዚአብሔር ልጅ መባሉ አልተለወጠምና ። " ድርሳነ ቄርሎስ ንባቡና አንድምታ ትርጓሜ !

✍ እግዚአብሔር አብ "የምወደው የማፈቅረው ልጄ ይህ ነው" ማቴ. 3÷17 ሲል መለኮቱን ከትስብእቱ ሳይለይ "ይህ ነው" አለ እንጂ መለኮቱን ከሰውነቱ ለይቶ
"በዚህ ትስብእት ውስጥ ያደረው መለኮት ልጄ ነው " አላለም።

✍ ወንጌላዊው ዮሐንስም በተዋህዶ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ የሆነውን ጌታ "ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ አምላክ እና የዘለዓለም ሕይወት ነው " አለ እንጂ።
1ኛ ዮሐ. 5÷20 "በኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነት ውስጥ ያደረው መለኮት የ እግዚአብሔር ልጁ ...." አላለም ።
ተዋህዶ ማለት ይህ ነውና ።

✍ ብፁዕ ጳውሎስም "በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን" ኤፌ. 2÷10 ሲል የመለኮት ባሕርይ ገንዘብ ያደረገውን የሰውነቱን አምላክነት ÷ ፈጣሪነት ነገረን እንጂ መለኮቱን ከሰውነቱ ለይቶ "በክርስቶስ ኢየሱስ ሰውነት ውስጥ ባደረው መለኮት ተፈጠርን " አላለም ።

✍ መለኮት ዘመን የማይቆጠርለት ቀዳማዊ ነው ÷ ሰውነት ግን ዘመን የሚቆጠርለት ደኃራዊ ነው ። ታዲያ ይህ ዘመን የሚቆጠርለት ሰውነት ዘመን ከማይቆጠርለት መለኮት ጋር ሲዋሀድ የመለኮትን ባሕርይ ገንዘብ በማድረጉ "ዘመን የማይቆጠርለት ÷ ጥንታዊ እና ቀዳማዊ ሆነ"

✍ ባለቤቱ ክርስቶስም "እውነት እላችኋለሁ እኔ ከ አብርሃም በፊት ነበርኩ " ዮሐ. 8÷58 ሲል ተዋህዶውን ነገረን÷ የለበሰው ሥጋ የቀዳማዊ መለኮትን ባሕርይ ባሕርይው በማድረገ ቀዳማዊ መሆኑን አስረዳን ።

✍ ለ ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስም በተገለጠለት ጊዜ "አነ ውእቱ ቀዳማዊ ወ አነ ውእቱ ደኃራዊ ÷ አነ ውእቱ አልፋ ወ ዖ" /ቅድመ ዓለም የነበርኩኝ ፊተኛው እና ዓለምን አሳልፌ የምኖር ኋለኛው ÷ መጀመሪያው እና መጨረሻው እኔ ነኝ / ራእይ. 1÷17 ብሎ ተዋህዶውን ነገር አስረዳን ።
✍ ደራሲውም "ሰላም ለልደቶከ ኦ አማኑኤል
ዘቀዳሚ ወዘደኃሪ ብሉየ መዋዕል " / መጀመሪያው እና መጨረሻው የሆንክ የዘመናት ባለቤት አማኑኤል ሆይ ለልደትህ (ለመወለድህ) ምስጋና ÷ ሰላምታ ÷ ክብር እና ስግደት ይሁን " አለ ።

✍ "ሥጋ ከ አብ የተገኘ ቃል ነው ÷ ቃልም ከ
ማርያም የተገኘ ሥጋ ነው " ቅ. ቄርሎስ
✍ ሰው ሲሆን የ እግዚአብሔር ልጅ መሆኑ
እንዳልተለወጠ ሲነግረን ሰው ከሆነ
በኋላም ከ ድንግል በተወለደው ሁለተኛ
ልደቱም የማይለወጥ የእግዚአብሔር ልጅ
መሆኑን ሲያስረዳንም
✍ "እግዚአብሔር ይቤለኒ ወልድየ አንተ ወአነ ዮም ወለድኩከ" /እግዚአብሔርም አለኝ አንተ ልጄ ነኅ እኔም ዛሬ ወለድኩህ " መዝ. 2÷7
ይሄ ለቀዳማዊ ልደቱን ሳይሆን ለሁለተኛ ልደቱ የተነገረ ነው ÷ ይህ ቃል የዳዊት መዝሙር
"ከ አብ ለተወለደው ልደቱ ሳይሆን ከድንግል ለተወለደው ልደት የተነገረ ነው ÷
ዘመን ለማይቆጠርለት ያለ እናት ከ አብ ለተወለደው ልደት ሳይሆን ÷ ዘመን ለሚቆጠርለት ያለ አባት ከ ድንግል ለተወለደው ልደት የተነገረ ነው ÷
ለመለኮታዊ ልደቱ ሳይሆን ለ ሥጋዊ ልደቱ የተነገረ ነው " ቅ.ቄርሎስ

ስብሐት ለ እግዚአብሔር!

ታኅሳስ 16/2018 ዓ.ም

ይበላል ወይስ አይበላም?? በ2018 ዓ.ም የጌታችን ልደት (ጌና) ረቡዕ ቀን ይውላል።  ብዙ ምዕመንም በሁለት ጎራ ተከፍሎ ግማሹ ይበላል፣ ግማሹ ደግሞ አይበላም የሚል ክርክር የተጀመረው የነ...
23/12/2025

ይበላል ወይስ አይበላም??

በ2018 ዓ.ም የጌታችን ልደት (ጌና) ረቡዕ ቀን ይውላል። ብዙ ምዕመንም በሁለት ጎራ ተከፍሎ ግማሹ ይበላል፣ ግማሹ ደግሞ አይበላም የሚል ክርክር የተጀመረው የነቢያት ጾም (የጌና ጾም) በገባ ገና በሳምንቱ ነበር። አሁን ደግሞ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል እየቀረበ ሲመጣ ክርክሩም ከበፊቱ የባሰ ውርርድን ሁሉ ጨምሮ ሲመጣ ባይ የማውቃትን የአቅሜን ይችን ልጽፍ ግድ አለኝ።

በመጀመሪያ ጌና (ልደት) ረቡዕ ወይም አርብ ሲውል ይበላል ወይ ለሚባለው አዎ በደንብ ይበላል ነው መልሴ። ምክንያቱም የቤተክርስቲያኗ መጽሐፍ (መጽሐፈ ስንክሳር) "ልደት (ጌና) አርብ ወይ ረቡዕ ቢውል ይበላል" ይላል፤ በልደት ቀን መጾም ሳይሆን በደስታ መብልና መጠጣት ይከበራል ነገር ግን በጾሙ ወቅት መብልን መገደብ እና ንስሃ ገብተን ቅዱስ ሥጋውንና እና ክቡር ደሙን ብንቀበል ደግሞ ለጌታችን ልደት የበለጠ ደስታን ይሰጠናል።

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትምህርት የጌና በዓል የደስታ ቀን በመሆኑ ረቡዕ ወይም አርብ ቢውልም የጾም ቀናት ቢሆኑም መብላት ይፈቀዳል። የሚበላበት ምክንያትም ከዘጠኙ ዓበይት የጌታችን በዓላት ሁለቱ ማለትም ልደትና ጥምቀትየዕዳ ደብዳቤያችን የተቀደደባቸው የድኅንነታችን መሠረት የተጣለባቸው ዓብይት በዓላት ስለሆኑ በመጾም፣ ራስን ከደስታ መገደብ ስለማይገባና በዓሉን በደስታ ለማሳለፍ መብልን መገደብ ስለማይገባ ነው።

በዓለ ልደት (ጌና ) ልክ እንደ ጥምቀት ጾም የገሃድ ጾም አለው። ግን ጾሙን ላልጾሙ የሚጾሙት የምትለው ቃል አይሰራም። ምክንያቱም የጌና ጾም ከሰባቱ አጽዋማት ጾም አንዱ በመሆኑ ማንኛውም ክርስቲያን ከ7 ዓመቱ ጀምሮ መጾም እንዳለበት ፍትሐ ነገሥት ያዛል። እና የጾም በላተኞች ይችን የአቋራጭ መንገድ እርሷት እላለው።

ልደት እና ጥምቀት በረቡዕና በዓርብ ቀን ከዋሉ አስቀድመን በዋዜማው ለውጥ አድርገን እንጾማቸዋለን ልደት ረቡዕ ከሆነ ማክሰኞ በዋዜማው፣ ዓርብ ከሆነ ሐሙስ በዋዜማው እስከ ምሽቱ አንድ ሰዓት (13 ሰዓት) እንጾማቸዋለን በሌሎችም ቀናት በዋዜማቸው በየዓመቱ ይጾማሉ።

የገሃድ ጾም ቀናቱ ሁለት ቢሆኑም ቁጥራቸው ግን ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ ተብሎ ይቆጠራል፡፡ በልደት አንድ ቀን፤ በጥምቀትም አንድ ቀን ሲሆን ሁለቱ ጾመ ገሃድ ይባላል።

የገሃድ ትርጉም፦

ጾመ ገሃድ ፦ ገሃድ እና ጋድ ተብሎ ይጠራል።

ገሃድ ፦ ማለት መገለጥ መታየት ማለት ነው። ይህም ተገለጠ ታየ የተባለውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህም አስቀድሞ አምላክነቱ የተገለጠባቸው ብዙ መንገዶችና ተአምራት ቢኖሩም በልደቱ ወልድ ሥጋ ለብሶ በአካል በመታየቱ እንዲሁም በጥምቀት የቅድስት ሥላሴ አንድነት ሦስትነት መገለጥ ፤ አብ በደመና ሆኖ የምወደው ልጄ ይህ ነው በማለት፣ ወልድ በባሕረ ዮርዳኖስ በመጠመቅ ፣ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ በመቀመጥ የክርስቶስ አምላክነት የተገለጠበት ዕለት ስለሆነ ገሃድ መገለጥ ተብሎ ተሰይሟል።

ጋድ ፦ ማለት ለውጥ ማለት ነው።

ልደትና ጥምቀት ረቡዕ ወይም ዓርብ ከዋለ ለውጥ ሆኖ የሚጾምበት ማለት ነው። ስለዚህ ገሃድ ስንል የክርስቶስ የሰውን ሥጋ ለብሶ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑ በዕለተ ልደት፤ የሥላሴ አንድነትና ሦስትነት በዕለተ ጥምቀት መገለጥ ፤ ጋድ ስንል ደግሞ ለዓርብና ለረቡዕ ጾም ለውጥ ሆኖ የሚጾመውን ጾም ማለታችን ነው፡፡

✅ ይህንን ጾም ጥር ዐሥር(10) ቀን የሚነበበው ስንክሳር እንዲህ ሲል ይገልጸዋል፡፡

" ወበእንተዝ አዘዙነ አበዊነ ከመ ይደሉ ንጹም እሎንተ ክልኤተ ዕለታተ ዘእምቅድመ በዓለ ልደት ወበዓለ ጥምቀት እስመ እላ ዕለታት ህየንቴሆሙ ለረቡዕ ወዓርብ ሶበ ይከውን ላዕሌሆሙ በዓለ ልደት ወጥምቀት ወበዝንቱ ይትፌጸም ለነ ክልኤቱ ግብር ግብረ ጾም ወግብረ በዓል ወከመዝ ሥሩዕ ውስተ አብያተ ክርስቲያኖሙ ለግብፃውያን ወለእመ ኮነ ዕለተ በይረሙን ዘውእቱ አስተርእዮ በዕለተ እሑድ አው በዕለተ ሰንበተ አይሑድ ይጹሙ በዕለተ ዐርብ እምቅድሜሁ እስከ ምሴት በከመ ተናገርነ ቅድመ ወለእመ ኮነ በዓለ ልደት ወበዓለ ጥምቀት በዕለተ ሰኑይ ኢይትከሀል ከመ ይጹሙ በዕለተ ሰንበት ዳዕሙ ይትዐቀቡ እምነ በሊዕ ጥሉላተ፡፡

ስለዚህ ከልደትና ከጥምቀት በዓል በዋዜማ ያሉትን ሁለቱን ዕለታት እንድንጾም አዘዙን። የልደትና የጥምቀት በዓል በረቡዕና በዓርብ ላይ በሚሆን ጊዜ በረቡዕና በዓርብ ፈንታ እንድንጾማቸው ይገባልና። በዚህም ሁለት ሥራ ይፈጸምልናል የጾም ሥራና የበዓል ማክበር ሥራ ነው። እንዲሁም በግብፃውያን አብያተ ክርስቲያን የተሠራ ነው በይረሙን (መገለጥ፣ ገሀድ) በእሑድ ወይም በአይሁድ ሰንበት ቀን ቢሆን ይህም ጌታ የተገለጸበት ጥር ዐሥር ቀን ነው በዋዜማው ዓርብ እስከምሽት ይጹሙ አስቀድመን እንደተናገርን ጥሉላትን ከመብላት ይጠበቁ በማለት ይገልጸዋል፡፡"

በዋዜማው እስከ 13 ሰዓት(እስከ ምሽቱ አንድ ስዓት) ተጹሞ ረቡዕ እና ዓርብ የጥላሉት ምግብ በበዓለ ሃምሳ የሚበላውን(ሥጋ፣ ቅቤ፣ እንቁላል.....)እንዲበላ መጽሐፍ ስንክሳር ያዛል።

✅ ጥምቀት ወይም ልደት እሑድና ቅዳሜ ከዋሉ ጾሙ መጀመር ያለበት ዓርብ ነው። ከሰኞ እስከ ዓርብ እስከ አንድ ሰዓት፣ ቅዳሜ እስከ ስድስት፣ እሑድ እስከ ቅዳሴ መውጫ እስከ ሦስት በመቁጠር የጾሙን ሰዓት 13 ሰዓት ያደርጉታል። ቅዳሜ እስከ ስድስት ለመጾሙም ሃይ ምዕ 20 ተጠቃሽ ነው።

በሌላ በኩልም ጋድ አንድ ቀን ነው ሰኞ ሲሆን እሑድን ብቻ ከጥሉላት እንከለከላለን እንጅ ቅዳሜን አይጨምርም፡፡

ጾመ ልደትን (ገና) በተመለከተ ፍትሐ ነገሥት እንዲህ ብሏል

የልደት (ገና) ጾም መግቢያው እና መውጫው

«...መጀመርያው የኅዳር እኩሌታ ፋሲካው የልደት በዓል ነው» / ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15፣ ቁ 568 ገጽ 150/፡፡

በዓለ ልደት እና ጥምቀት ረቡዕ እና ዓርብ ቢውሉ ደግሞ
"...የረቡዕን እና የዓረቡን ጾም ግን ከልደት፣ከጥምቀት እና ከበዓለ ሃምሳ በቀር፤ ዘወትር ይጹሙ (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15፣ቁ 603 ገጽ 156)

" የጥምቀት እና ልደት በዓል በረቡዕ ወይም ዓርብ ከዋለ በዋዜማው ጾመው በዓሉን በደስታ ያከብሩ " ይላል።( ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15 ፥ 566)

የገና ጾም ቀናት ብዛት፦

ጋድ አንድ ነው እሱም የጥምቀት ዋዜማ ብቻ ነው የልደት ዋዜማ የለውም የሚሉም አሉ። እንዲህ ለሚሉት የጾመ ነቢያት ቁጥር ማሳወቅ ተገቢ ነው።

ጾመ ጋድ አንድ ነው ይህም በበዓለ ልደት ዋዜማ የምንጾመው ጋድ መሆኑን ሁሉም የሚያውቀው ሃቅ ነው፡፡

✅ የ ቀናት አቆጣጠሩ፦

◉ ከኅዳር 15 - 30 ➝ 15 ቀናት
◉ በታኅሣሥ ወር ➝ 29 ቀናት
◉ ድምር 15 + 29 = 44 ቀናት ይሆናል።

➝ 40ው ቀናት የነቢያት/የገና ጾም
➝ 3ቱ ቀናት የአብርሃም ሶርያዊ ተራራ ያፈለሰበት ጾም
➝ 1ዱ ቀን የገሃድ ጾም ነው። በጠቅላላው 44 ቀን ጾመ ነቢያት/ገና ይጾማል።

+++ ስብሐት ለ እግዚአብሔር ይቆየን +++

Address

Square
Addis Ababa
1000

Telephone

+251913409143

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Tewahido Haymanote posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to Tewahido Haymanote:

Share