06/03/2026
ክፍል 3
ጦርነት፣ ቸነፈር፣ ረሐብና የምድር መንቀጥቀጥ (መናወጥ)
የሱስ ደቀመዛሙርቱን እንዲህ ሲል አስጠንቅቋቸዋል፡- “ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፥ አትደንግጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው። ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣልና ፤ ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል፡፡” (ማቴዎስ 24:6, 7)፡፡
ከቅርብ ጊዜ ውስጥ ህዝቦች የኖሩባቸውን ኹከትና ብጥብጥ ተመልከተናል፡፡ እያንዳንዱ ሰው ሰላምን ሲያንጋጥጥ፣ በተቃራኒው ጦርነት እየፈነዳ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎችን ህይወት እየቀጠፈ ይገኛል፡፡ በብዙ ሀገራት በብሺ የሚቆጠሩ ስደተኞች ያለቀያቸውና አገራቸው እንዲሰደዱ እያደረጉ የሚገኙት ጦርነቶችና የፖለቲካ ነውጦች ረሃብ፣ ስቃይና ረሃብ እያደረሱባቸው ይገኛል፡፡ ምንም እንኳ እነዚህ ዘግናኝ ውድመቶች ቢደርሱም፣ ጦርነቱን ለማስቀጠል የጦር መሳሪያዎችንና ተተኳሽ ጥይቶችን ለመግዛት ቢሊዮን ዶላሮች እየፈሰሱ ናቸው፡፡
ከዚህ በተቃራኒው፣ በአንዳንድ ሀገራት ምግብ ተትረፍርፎ ብዙ ህዝቦችም በሚመገቧቸው ፈጥነው በሚበስሉ (fast food) ወይም ግብስብስ ምግቦች (junk food) ምክንያት በበሽታ እየተጠቁ እና በብዙ ሺህ ቶን የሚመዘን ምግብም ተመጋቢ አጥቶ በየቀኑ በቆሻሻ መጣያ እየተደፋ ቢሆንም፣ በአንፃሩ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ህዝቦች በረሃብ የተነሳ በሞት እየተቀጠፉባቸው ያሉ ሀገራትም ይገኛሉ፡፡ ቴክኖሎጂ እንዲህ በዘመነበት፣ ቁሳቁሶችን በቀላሉ የሚጓጓዙበት ትራንስፖርት እንዲህ በቀለለበት በዚህ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ይህን መቀበል በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ በተጨማሪም ንፁህ ውኃ ባለመጠጣት ወይም የሚቀመስ ምግብ በማጣት በሚደርስባቸው ድካም የተነሳ የሰው ህይወት የሚቀጠፍባቸው ሀገራትም አሉ፡፡ በቅርብ አስርት ዓመታት ውስጥ እየደረሱ ያሉት የተፈጥሮ አደጋዎችም (መቅሰፍቶችም) የሱስ ከጠቀሳቸው ምልክቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ በምንኖርባት ምድር አንዳንድ ሀገራት ህይወትን ሙሉ በሙሉ እያወደሙ ያለው ድርቅ እንዳለ ሆኖ፣ ያለመጠን ከተፈጥሮው በላይ በሚዘንበው ዝናብ ምክንያት እየተከሰተ ያለው ጎርፍ፣ ማዕበል ወይም አውዳሚ አውሎነፋስ ብዙ የሰው ህይወትንና የንብረት ውድመትን አስከትለው ያልፋሉ፡፡ በቅርብ ዓመታት ውስጥ፣ በብዙ ቦታዎች እየተከሰተ ያለው የምድር መናወጥ (መንቀጥቀጥ) የኃይሉ መጨመር ብቻ ሳይሆን እያደሰ ያለው ጉዳትም ይህ ነው ተብሎ አይገለጽም፡፡
“የመሬት መናወጥና ማዕበል፣ የውኃ ሙላትና የእሳት አደጋዎች፣ በንብረትና በሰው ሕይወት ላይ የሚያደርሱትን ውድመት የምንሰማው ምን ያህል ነው! እነዚህ ጥፋቶች ከሰው ቁጥጥር ውጭ መሆናቸው ግልጥ ነው፡፡ ነገር ግን በሁሉም የእግዚአብሔር እቅድ አለበት፡፡ ከቁጥጥር ውጭ በሆኑ የተፈጥሮ ኃይላት ፍንዳታ፣ ሙሉ በሙሉ ከሰው ቁጥጥር ውጭ በሆኑ ነገሮች የሚፈጠሩ መሆናቸው እርግጥ ነው ፤ ይሁን እንጂ በእነዚህ ሁሉ ነገሮች የእግዚአብሔር ዓላማ መነበብ ይችላል፡፡ ሰዎች ሊደርስባቸው የሚችለውን አደጋ እንዲገነዘቡ ለማድረግ ከሚጠቀምባቸው ወኪሎች መካከል ናቸው፡፡”
ተመራማሪዎች እና ፈላስፋዎች፣ እያንዳንዱ አደጋ የአየር ንብረት በተፈጥሮ ላይ በሚያስከትለው ለውጥ የተነሳ የሚመጣ ውጤት ነው ብለው ማብራሪያ ለማግኘትና ክስተቶቹንም (አደጋዎቹንም) ማስወገድ የሚችሉበትን መፍትሔ ፍለጋ በመጣጣር ላይ ናቸው፡፡ አሁንም በድጋሜ ሰብዓዊ ጽንሰ-ሐሳቦች (ፍልስፍናዎች) ለእነዚህ ክስተቶች ሊኖር ከሚገባው ከእውነተኛው ምክንያት የሰዎችን ጀሮ በማጣመም ላይ ናቸው፡፡ ተፈጥሮ በሰብዓዊ ክፉ ተግባር የተነሳ መሰቃየቷ እና መመሰቃቀሏ እውነት ነው ፤ ይሁን እንጂ ክርስቶስ የዘረዘራቸው ምልክቶች እነዚሁ መሆናቸውንም መርሳት የለብንም፡፡እንዲሁም ምድርን ያወደሙ ሰዎች ባደረሱት ውድመት የተነሳ እነርሱም መሰቃየት የግድ እንደሚላቸውም ጭምር ልንረሳ አይገባም፡፡
“አሕዛብም ተቈጡ፥ ቍጣህም መጣ፥ በሙታንም ትፈርድ ዘንድ ዘመን መጣ፥ ለባሪያዎችህም ለነቢያትና ለቅዱሳን ስምህንም ለሚፈሩት ለታናናሾችና ለታላላቆችም ዋጋቸውን ትሰጥ ዘንድ፥ ምድርንም የሚያጠፉትን ታጠፋ ዘንድ ዘመን መጣ ” (ራዕይ 11:18)፡፡
ታላቁ የመፍጠር ሥራ ውጤቶች በመውደም ላይ ናቸው ፤ ለውድመቱ ኃላፊነቱን የሚወስዱትም ይቀጣሉ፡፡ ክርስቶስ ጊዜውን እንዴት አድርገው ለይተው ያውቁ ዘንድ ለደቀመዛሙርቱ የገለፀላቸው እነዚህ ክስተቶች (ሁነቶች)፣ የመገለጡ ምልክቶች ሊሆኑ ይችላሉ? አወ ፤ ናቸው፡፡ ደቀመዛሙርቱ የዘመኑ መጨረሻ መቼ ነው ? ብለው እንደጠየቁት ፤ እኛም ቀናትን መወሰን አንችልም ፤ ምልክቶችን ብቻ ልንተረጉማቸው እና ለዓለማችንና ለነዋሪዎቿ ከዚህ በላይ ብዙ ጊዜ እንደማይኖር ልናስተውል እንችላለን፡፡ “ስለዚያች ቀንና ስለዚያች ሰዓት ግን ከአባት ብቻ በቀር የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ፣ ሰውም ቢሆን የሚያውቅ የለም፡፡” (ማቴዎስ 24:36)፡፡
ታሪክ ራሱን ይደግማል
የመጨረሻው ዘመን በምድር ላይ ከወረደው ጎርፉ በፊት ከነበረው ሁናቴ ጋር ተመሳሳይ እንደሚሆን የሱስ አስቀድሞ አመላክቷል፡፡ “ስለዚያች ቀንና ስለዚያች ሰዓት ግን ከአባት ብቻ በቀር የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ ሰውም ቢሆን የሚያውቅ የለም። የኖኅ ዘመን እንደነበረ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይሆናልና።
በዚያች ወራት ከጥፋት ውኃ በፊት፥ ኖኅ ወደ መርከብ እስከገባበት ቀን ድረስ፥ ሲበሉና ሲጠጡ ሲያገቡና ሲጋቡም እንደ ነበሩ፣ የጥፋት ውኃም መጥቶ ሁሉን እስከ ወሰደ ድረስ እንዳላወቁ፥ የሰው ልጅ መምጣት ደግሞ እንዲሁ ይሆናል።” (ማቴዎስ 24:37–39)፡፡
መብላት፣ መጠጣት ወይም መጋባት የኃጢአት ተግባራት አይደሉም፡፡ እነዚህ ነገሮች ለእግዚአብሔር አስፀያፊ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ነገር ቢኖር ሰው ያለገደብ እየፈፀማቸው መሆኑ ነው፡፡ በዛሬው ጊዜ በጣም የታወቁ በሽታዎች የተንሰራፉበት ምክንያት በአብዛኛው በመጥፎ አመጋገብ ወይም አጠጣጥ፣ አካላዊ እንቅስቃሴ በሌለው የህይወት አኗኗር፣ እንዲሁም ለጤና ጎጂ የሆኑ ንጥረ ነገሮችን በመጠቀምና አካልን ከመበዝበዝ የተነሳ የተከሰቱ ናቸው፡፡ መርዛማ ንጥረ ነገሮችን ማለትም በታላላቅ ከተሞች ወደ ትንፋሽ እየገባ ያለው አየር ወይም ትንባሆንና ሱስ አምጭ ንጥረ ነገሮችን (ጎጂ መድሃኒቶችን) በመጠቀም ለረዥም ጊዜ ተጋላጭ መሆን፣ ለብዙ በሽታዎች መንስኤ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን፣ ነገር ግን ሥነ-ባህርያዊ (የሥነ-ትውልድ) መለዋወጥን ሞራለ ቢስ ልሽቀት ወይም በሽታ ተከላካይ ህዋሳትን (ሴሎችን) አጥቂ በሽታ እንዲፈጠር አድርጎታል፡፡ በሰዶምና በጎሞራ የተፈፀመው ታሪክ፣ እንዲሁም ከተስፋዋ ምድር ፊት ለፊት በሰጢም ሸለቆ የእስራኤል ልጆች ያለፉበት የውድቀት ተሞክሮ፣ ሴሰኝነት እና መሻትን ያለመግዛት ልቅ ፍላጎት፣ ከምናስበው በላይ፣ እጅግ አፀያፊ ኃጢአት በእግዚአብሔር ፊት እንዲፈጽሙ ሰዎችን የሚመሩ መሆናቸውን እኛን ለማስተማር የተመዘገቡ ማስጠንቀቂያዎች ናቸው፡፡
“ በስሜት እርካታ ቋጥኝ ላይ ተንኮታኩተው ሆጭ እንዳሉ የተተው፣ የተበታተኑ፣ በዘመናት ዓመታት ሁሉ የባህርይ ስብርባሪዎች ሞልተዋል፡፡ ወደምድር ታሪክ መዝጊያ እየተቃረብን ስንመጣና የእግዚአብሔር ህዝቦች ሰማያዊውን ከንዓን መግቢያ ደንበር ላይ ሲደርሱ፣ ሰይጣን ጥንት ካደረገው ኃይሉን በእጥፍ አሰባስቦ ወደ አምላካዊው መልካም ምድር እንዳይገቡ ይከላከላቸዋል፡፡ በእያንዳንዱ ሰው መንገድ ላይ ወጥመዱን ይዘረጋል፡፡ ከፈተናዎቹ መከለል (መጠበቅ) ያለባቸው ያልተማሩትና እውቀት የሌላቸው ብቻ አይደሉም ፤ ይልቁንም በኃላፊነት ከፍተኛ ቦታ ላይ አልፎም በተቀደሰው መንፈሳዊ ስፍራ እያገለገሉ ለሚገኙት ሁሉ ፈተናዎቹን አቀነባብሮ ያቀርብላቸዋል፡፡ እነዚህን ሰዎች በማሳት ነፍሳቸውን መበከል ከቻለ በእነርሱ አማካኝነት ብዙዎችን ማጥፋት ይቻለዋል፡፡ ለዚህም ሰይጣን ከሶስት ሺህ ዓመታት በፊት የተጠቀመውን ያንውን ወኪል (ዘዴ) አሁንም ጥቅም ላይ ያውለዋል፡፡ ዓለማዊ ጓደኞችን፣ ውበትና ቁንጅናን፣ ደስታና ፈንጠዝያን፣ ሳቅና ጨዋታን፣ ግብዣና የወይን ጠጅን ተጠቅሞ ሰዎች ሰባተኛውን ሕግ እንዲጥሱ ይፈትናቸዋል፡፡”