14/02/2026
የሲርለና በጎ አድራጎት ድርጅት ለ1 ሺህ ቤተሰቦች የረመዳን የአስቤዛ ድጋፍ አበረከተ!
- የካቲት 7 ቀን 2018 ዓ.ል
የሲርለና የበጎ አድራጎት ድርጅት የታላቁን የረመዳን ወር ፆምን በማስመልከት፣ በተለያየ ምክንያት በችግር ውስጥ ለሚገኙ 1,000 ቤተሰቦች የአስቤዛ ድጋፍ ማድረጉን አስታወቀ።
በኡስታዝ ኑሩ ቱርኪ የሚመራው ይህ ድርጅት ድጋፉን ሊያበረክት የቻለው፣ በቅርቡ በማኅበራዊ ሚዲያ (በተለይም በቲክቶክ) ለአራት ቀናት ባካሄደው የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር አማካኝነት መሆኑ ተገልጿል።
በዕለቱ ድጋፍ ከተደረገላቸው ወገኖች መካከል 315 የሚሆኑት የክርስትና እምነት ተከታዮች መሆናቸውንም ኡስታዝ ኑሩ ቱርኪ ገልጸው፤ ለዚሁ በጎ ተግባር ስኬት አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት በሙሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ድርጅቱ በአሁኑ ወቅት ወላጅ አልባ ሕፃናትን (የቲሞችን)፣ አረጋውያንን፣ ምስኪኖችንና ለችግር ተጋላጭ የሆኑ ወገኖችን ጨምሮ በቀጥታ ድጋፍ የሚያደርግላቸው ቤተሰቦች ቁጥር 1,700 መድረሱ ታውቋል።
የሲርለና በአሁኑ ወቅት ሥራዎቹን እያከናወነ የሚገኘው በኪራይ ቤት ውስጥ በመሆኑ፣ የሚመለከተው የመንግሥት አካል ድርጅቱ የሚሠራቸውን ዘርፈ-ብዙ የበጎ አድራጎት ተግባራት ከግምት ውስጥ በማስገባት ቋሚ የሆነ የመሥሪያ ቦታ እንዲሰጠው ጥሪ ቀርቧል።