24/05/2026
ለአላህ ብሎ መዋደድ
ሙስሊሞች እንደ ማህበረሰብ ብሎም እንደ ኡማ ጥንካሬያቸውንና የተሟላ ማንነታቸውን አስጠብቀው ዘውታሪ ወደሆነ ስኬትና ሀሴት መዝለቅ እንዲችሉ ሊከተሏቸው የሚገቡ መርሆዎች አሉ። ከነዚህ ወሳኝ መርሆዎች መካከል መልካም የሆነ የእርስ በርስ ትስስር እና መለኮታዊ መስፈርት ላይ የተገነባ ግንኙነት መሆኑ ግልጽ ነው። በተለይም የሙስሊሞች ህይወት ምንጭ ኢስላም እንደመሆኑ የህይወታቸው መልካም ዋስትና
ለአላህ ብለው መዋደዳቸው እና መረዳዳታቸው ነው።
በአላህ መንገድ ወንድማማችነት እጅግ የተቀደሠ የአላህ ሱብሃሁ ወተዓላ ስጦታ፣ አንፀባራቂ የሆነ የጌታ ሽልማት እና ታላቅ አምላካዊ ፀጋም ነው። ይህን ፀጋ ማንም ተራ ሰው አያገኘውም። የትኛውም ሰው በቀላሉ አይታደለውም። አላህ ሱብሀነሁ ወተዓላ ከባሮቹ መካከል እሱን አጥርተው ለሚገዙ የሚሠጠው ነው። ከወዳጆቹም መካከል ለመረጣቸው የሚያወርሰው እንጂ ሌላ አይደለም። ከፍጥረታቱም ውስጥ እጅግ ፅዱ
ልቦና ባላቸው ሰዎች ቀልብ ውስጥ ይህ ችሮታ ያኖረዋል።
አላህ ሱብሀነሁ ወተዓላ በሱረቱል ዓሊ ዒምራን
ላይ እንዲህ ይለናል
ﻭَﺍﻋْﺘَﺼِﻤُﻮﺍ ﺑِﺤَﺒْﻞِ ﺍﻟﻠَّﻪِ ﺟَﻤِﻴﻌًﺎ ﻭَﻟَﺎ ﺗَﻔَﺮَّﻗُﻮﺍ
ﻭَﺍﺫْﻛُﺮُﻭﺍ ﻧِﻌْﻤَﺖَ ﺍﻟﻠَّﻪِ ﻋَﻠَﻴْﻜُﻢْ ﺇِﺫْ ﻛُﻨﺘُﻢْ ﺃَﻋْﺪَﺍﺀً
ﻓَﺄَﻟَّﻒَ ﺑَﻴْﻦَ ﻗُﻠُﻮﺑِﻜُﻢْ ﻓَﺄَﺻْﺒَﺤْﺘُﻢ ﺑِﻨِﻌْﻤَﺘِﻪِ
ﺇِﺧْﻮَﺍﻧًﺎ ﻭَﻛُﻨﺘُﻢْ ﻋَﻠَﻰٰ ﺷَﻔَﺎ ﺣُﻔْﺮَﺓٍ ﻣِّﻦَ ﺍﻟﻨَّﺎﺭِ
ﻓَﺄَﻧﻘَﺬَﻛُﻢ ﻣِّﻨْﻬَﺎ ۗ ﻛَﺬَٰﻟِﻚَ ﻳُﺒَﻴِّﻦُ ﺍﻟﻠَّﻪُ ﻟَﻜُﻢْ ﺁﻳَﺎﺗِﻪِ
ﻟَﻌَﻠَّﻜُﻢْ ﺗَﻬْﺘَﺪُﻭﻥَ
“የአላህንም (የማመን) ገመድ ሁላችሁም ያዙ። አትለያዩም። ጠበኞችም በነበራችሁ ጊዜ በእናንተ ላይ (የዋለውን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ።በልቦቻችሁም መካከል አስማማ። በጸጋውም ወንድማማቾች ኾናችሁ። በእሳት ጉድጓድ አፋፍም ላይ ነበራችሁ። ከእርስዋም አዳናችሁ። እንደዚሁ ትመሩ ዘንድ አላህ ለእናንተ አንቀጾቹን ያብራራል።” (አል ኢምራን፤ 103)
ወንድማማችነት ኢስላማዊው የእምነት አመላከከት /ዐቂዳ/፣ የኢማን እና የአላህ ፍራቻ ውጤት ከሚያስተሣስር ማንኛውም ሙስሊም ጋር በጥብቅ የሚያቆራኝ ከውስጥ የሆነ ጥልቅ የመተዛዘን፣ የመዋደድ፣ የመካባበርና የመተማመን ስሜትን የሚያወርስ ኢማናዊ ጥንካሬ ነው። ይህ ወንድማዊ ስሜት እየጎለበተ ሲሄድ በአንድ አማኝ ልብ ውስጥ በጎ የሆነ ጥልቅ ስሜትን ይፈጥራል። መረዳዳትና ሌላውን ከራስ አስበልጦ መውደድ፣ ለሌላው መቆርቆር፣ መተዛዘን፣ ይቅር መባባል፣ በችግር ጊዜ መደራረስ፣ በድካም ጊዜ መተጋገዝና የመሣሰሉት.. ከበጎ ውጤቶቹ መካከል ከብዙ በጥቂቱ የሚጠቀሱ ናቸው። እውነተኛ የወንድማማችነት ስሜት በሰው ልጆች ነፍስ፣ ንብረትም ሆነ ክብር ላይ ከሚደርሰው ማንኛውም ጉዳት አንፃር የተቃዋሚነት አቋምም ለመያዝ ያስችላል። በአላህ መንገድ ወንድማማችነት ከኢማን ጋር እጅግ የተቆራኘ ባህሪ ነው። ከአላህ ፍራቻ ጋርም በእጅጉ የተዛመደ ነው። ያለ ኢማን ወንድማማችነት እንደማይኖር ሁሉ ያለ ወንድማማችነትም ኢማን የለም። ያለ አላህ ፍራቻ የልብ ጓደኝነት እንደማይኖር ሁሉ ያለ የልብ ጓደኝነትም የአላህ ፍራቻ የለም። በሌላ አነጋገር “በአላህ መንገድ ወንድማማችነት ኢማንን መሠረት ያደረገ ነው። ሰዎች ለወንድማማችነታቸው ትኩረት የማይሠጡ ከሆነ ኢማናቸው ያጠራጥራል።” እንደማለት ነው። እንዲሁም “ሰዎች አላህን ፍራቻ መሠረት አድርገው የልብ ጓደኛ መያዝ አለባቸው። የልብ ጓደኝነት ከሌለም የአላህ ፍራቻ የለም” ማለት ነው።