08/06/2026
በብፁዕ ጠቅላይ ዋና ሥራ አስኪያጅ የተመራ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ልዑክ የተለያዩ የግንባታ ፕሮጀክቶችን ጎበኘ።
ሰኔ 01 ቀን 2018 ዓ.ም. Miidiyaa Shaggar/ሸገር ሀገረ ስብከት ሚዲያ/
በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የተመራ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች ልዑካን ቡድን፤ በፒያሳ ልዩ ስሙ አሮጌ ቄራ እና በጠቅላይ ቤተ ክህነት አካባቢ በግንባታ ላይ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዘመናዊ ሕንጻዎች ጎበኘ።
የጉብኝቱ ዋና ዓላማ የሕንጻዎቹ የግንባታ ሂደት አፈጻጸም ምን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ለመገምገምና እያጋጠሙ ያሉ ማነቆዎችን በመለየት መፍትሔ ለመስጠት መሆኑ ተገልጿል። ብፁዕነታቸው በሁሉም የግንባታ ቦታዎች በአካል በመገኘት የሥራውን ሂደትና ጥራት በጥንቃቄ የተመለከቱ ሲሆን፣ የየፕሮጀክቶቹ ተቋራጮችም (ኮንትራክተሮች) እስካሁን የተከናወኑ ተግባራትንና ያጋጠሟቸውን ተግዳሮቶች በተመለከተ ሰፊ ማብራሪያና ገለጻ አድርገውላቸዋል።
የግንባታው ተቋራጮች በገለጻቸው ወቅት፤ ብፁዕነታቸው በተደጋጋሚ እስከ ሳይቶቹ ድረስ በመገኘት የሚያደርጉት ቀጣይነት ያለው ክትትልና ድጋፍ ለሥራው መፋጠንና ለጥራቱ መጠበቅ ትልቅ መነቃቃትን የፈጠረ መሆኑን ገልጸው፣ እያጋጠሟቸው ያሉ ወቅታዊ ችግሮች እንዲቀረፉላቸው ጠይቀዋል።
ብፁዕነታቸውም ከተቋራጮቹ የተነሱትን አበይት ችግሮች ካደመጡ በኋላ፣ የግንባታው ሂደት ሊከተለው ስለሚገባው ሥርዓትና መስተካከል ስለሚገባቸው ጉዳዮች አባታዊ የሥራ መመሪያና ምክር ሰጥተዋል። አክለውም፣ እየተገነቡ ያሉት ሕንጻዎች የቤተ ክርስቲያኒቱ የልማትና የዕድገት አካል በመሆናቸው ተቋራጮቹ ሥራውን እንደ ራሳቸው ንብረትና ኃላፊነት ሊቆጥሩት እንደሚገባ አሳስበዋል። በግንባታው ሂደት ላይ የሚገጥሙ ፈተናዎችን በጽናትና በብልሃት በማለፍ፣ የሕንጻዎቹ ግንባታ ጥራታቸውን ጠብቀውና በተቀመጠላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁም ብፁዕነታቸው አሳስበዋል።