04/04/2026
በህግ ጥላ ውስጥ ያለ ህገወጥነት
ፍትህ ሆይ ወዴት ነሽ?
በወር ከ60,000 ብር ወደ 320,000 ብ ር የሚያስጨምር ኢፍትሀዊነት ! በምን ስሌት ይሆን???!!!
በቅዱሳን ሀብት እና ጉልበት የተገነባውን የቤተክርስትያን ንብረት እንዲሁም የህዝብ ንብረት የሆነውን ዘመናዊ የአምልኮ አዳራሻችንን መንግስት እና ፍትህ ባለበት ሀገር በጠራራ ፀሀይ ፍትህን በማጣመም አጭበርብረው መነጠቃችን ሳያንስ በሥራ አፈጻጸማቸውና በሥነ-ምግባር ችግር አንቱታን ያገኙን በፍትህ ስርዓቱ ውስጥ የተሰገሰጉን ጥቂት ግለሰቦችን በተለያየ ነገር በመደለል ጭምር በወር 60 ሺህ ብር እንከፍልበት የነበረውን ቦታ 400% ጨምረው በወር 320 ሺህ ብር ሒሳብ ተሰልቶ እንድንከፍል በግፍ ተበይኖብናል። የትኛው የአዲስ አበባ ወይም የሀገራችን ክፍል 400% የኪራይ ጭማሪ የተደረገበት ቦታ እንዳለ እኛ አይገባንም ይሁንና አሁን ቤተ ክርስቲያን ላይ ግን ይህ ግፍ ተሰርቷል ያውም እራሷ በሰራችው አዳራሽ እና ቢሮዎች ማለት ነው።
ይህ አዳራሽ በሚገኝበት በተለምዶ ለም ሆቴል በመባል በሚታወቀው በቦሌ ክፍለከተማ ወረዳ 4 አካባቢ የሚገኙ እጅግ ቅንጡ የሆኑ የመኖሪያ አፖርትመንቶች እንዲሁም ቢሮዎች እንኳን ባለፉት 4 እና 5 አመታቶች ውስጥ ከ10% እና 30% በላይ የኪራይ ጭማሪ አለማድረጋቸው እሙን ሆኖ ሳለ፤ እኛ እራሳችን አዘምነን በገነባነው አዳራሽ ላይ ከአካባቢው ዋጋ እጅግ በተጋነነ መልኩ 60 ሺህ ብር እንከፍልበት የነበረውን ቦታ 400% ጨምረው በወር 320 ሺህ ብር ሒሳብ ክፈሉ መባላችን በፍትህ መንበር የተሰየሙት ዳኞች ከጥቅም ባለፈ ለእምነቱ ያላቸውን ጥላቻ ያንፀባረቁበት የበቀል በትር መሆኑን በገሀድ ያሳያል።
ምን ግዜም ለህግ ተገዢ የሆነችው የክብር ሕይወት ቤተክርስቲያንም የአገሪቱን ህግ እና የፍትህ ስርዓት ተማምና ይህን ሁኔታ በሕግ አግባብ በመከላከል ከመቆየት ውጪ ሌላ መንገድም ሆነ አማራጭ ሳትከተል ቆይታለች።
ሆኖም ይህ ሕጋዊ ሒደት እልህን አስከትሎ ሃሰተኛ የሰው እና የሰነድ ምስክር በማደራጀት በቅዱሳን ጉልበት እና ንብረት ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎበት የተሰራን አዳራሽ ምንም አዲስ ግንባታ አልተደረገም የሚል ብያኔን በመስጠት ያለምንም ካሳ በግፍ ከቤተክርስቲያኗ እንዲነጠቅ ከማድረጋቸው ባሻገር 60 ሺህ ብር እንከፍልበት የነበረውን ቦታ 400% ጨምረው በወር 320 ሺህ ብር ሒሳብ እንድንከፍል እስከመወሰን አድርሷቸዋል
አሁንም እኛ የክብር ሕይወት ቤተክርስቲያን ልጆች እና የወንጌል አማኞች
ፍትህ ሆይ ወዴት ነሽ?
የኢፌዴሪ ህገ መንግስት አንቀፅ 27 ሆይ ወዴት ነሽ? እያልን
እግዚአብሔርን ለሚፈሩ እና ፍትህን ለሚያከብሩ በመላው አገሪቱ ለሚገኙ ወገኖቻችን ነግ በእኔ ነውና ዘር ቀለም ሳንለይ የኃይማኖት ድንበር ሳይነጥለን ለእውነት እና ለፍትሕ ድምፅ እንድንሆን እንጠይቃለን!!!
ፍትህ እንፈልጋለን???