10/09/2025
"ዓመታትን በቸርነትህ ታቀዳጃለህ መዝ ፷፬÷፲፩"
"በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱሥ።
አሀዱ አምላክ አሜን!!!"
❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖ ❖
"እንኳን ለ፪ሺ፲፰ ዓ.ም ዘመነ ቅዱስ ማቆስ በሰላም አደረሳችሁ።"
🌻~ ዓመታት በቸርነትህ ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል። የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ፥ ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ። መዝ ፷፬፥፲፩
🌻~ ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ የመሸጋገሪያው ዕለት በየዓመቱ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ የዘመን መለወጫ፣ እንቁጣጣሽ፣ ሌላም መጠሪያ ስሞቹ ናቸው፡፡ በግእዝ ርእሰ ዐውደ ዓመትም ይባላል፡፡
~☆☆☆~
🌻~ እግዚአብሔር በልግስናው በስጦታው ምድርን በልምላሜ ወንዝንም በውሃ ተራሮችንም በፅጌያት ሰማያትን በከዋክብት ያደምቃቸዋል፤ ከግዜ ውጭ የሆነ ጌታ ዘመናትንም እስረጅቶ አዝማናትን ይተካል።
~☆☆☆~
🌻~ ቅዱስ ማርቆስ ወንጌሉን ሲጽፍ “የእግዚአብሔር ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል መጀመሪያ እነሆ መንገድህን የሚጠርግ መልእክተኛዬን በፊትህ
እልካለሁ፡፡ የጌታን መንገድ አዘጋጁ፡፡ ጥርጊያውን አቅኑ” እያለ “በምድረ በዳ የሚጮኸ ሰው ድምፅ” ተብሎ በኢሳይያስ እንደተነገረ የነቢዩ ዘካርያስ ልጅ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በዘመነ ብሉይ መጨረሻና በዘመነ ሐዲስ መጀመሪያ ላይ ተነስቶ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ!” እያለ ስለ ክርስቶስ አዳኝነት እየመሰከረ በምድረ በዳ የንስሐን ጥምቀት እያጠመቀ መጣ ብሎ ለዘመነ ወንጌል የመጀመሪያ ምዕራፍ ትምህርትና ተግሳጽ እንዳደረገው ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ ይነግረናል፡፡ ማር.፩፥፲፬ ኢሳ. ፵፥፫-፬
~☆☆☆~
🌻~ የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ ሆኖ መገኘቱን በመረዳት የቤተ ክርስቲያን አበው የበዓላትን ድንጋጌ በወሰኑበት አንቀጽ የመጥምቁ ዮሐንስ መታሰቢያ በዓል የኢትዮጵያ አዲስ ዓመት በሚከበርበት መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር በየዓመቱ የዘመኑ መጀመሪያ በእርሱ ስም እንዲጠራ እንደወሰኑ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ መጽሐፍ ይነግረናል፡፡ ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ ፩-፫
~☆☆☆~
🌻 ~ የዘመኑ መቀየር ከቁጥር በዘለለ የእኛውም አስተሳሰብ እንዲቀየር ነው፡፡ ለሥጋዊ ኑሮአችን መሳካት በእቅድ እንደምንመራው ሁሉ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን እናስብ፤ ቃለ እግዚአብሔር ለመማር፣ ንስሐ ለመግባት፣ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል መንፈሳዊ እቅድ እናውጣ! ተግባራዊ ለማድረግም ጥረት እናድርግ፡፡ አምላካችን ከእኛ ሕይወት ፍሬ ለማግኘት በልጅነታችን፣ በወጣትነትና በሽምግልና እድሜያችን ሦስት ጊዜ መጣ ፍሬ ሃይማኖትና ምግባር አጣብን አትክልተኞቹን ቅዱሳን መላእክትን “ ስለምን ደግሞ መሬቱን ታጎሳቁላለች?” ቢላቸው “ጌታ ሆይ ዙርያዋን እስክኮተኩትላትና ፋንድያ እስካፈስላት ድረስ በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት” እያሉ በለመኑት የብድር እድሜ ነው አዲስ ዓመቱን ለማየት የቻልነው። ሉቃ. ፲፫፥፲፯ በተሰጠን የብድር እድሜ መልካም ነገር ለመሥራት እንነሣ በስንፍና ያሳለፍነው ጊዜ ይብቃን! ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ እንዲህ ይለናል “የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት ጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና”። 1ኛ ጴጥ. ፬፥
☆☆☆
🌻 ~ ፪ሺ፲፰ ዓ.ም ብዙ ነገር ያየንበት የሰማንበት ያዘንበት እና የተጨነቅንበት ዘመን ነው። በተለይ ለኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች በአንድ በኩል ዓመቱን ሙሉ አሕዛብ እና መናፍቃን ዕረፍት በመንሳት አክራሪወቹ፦ በሰይፍ ሲያርዱን፤በድንጋይ ሲቀጠቅጡን፤ በእሳት ሲያቃጥሉን፤ መንግስት ሳይቀር አይቶ ፍትህን ሲነፍገን ፤ ጌታ በደሙ የሰጠንን የምህረት ዘመን ዓመተ ፍዳ አድርገውብን አልፈናል። ግን ፪ሺ፲፰ ዓ.ምህረትስ? ሥለሁሉም ነገር የዓለም መድኃኒት የድንግል ልጅ ይክበርና በቸርነቱ ጠብቆ ይኸው ለ ፪ሺ፲፰ ዓ.ም አደረሰን፤ በዕውነት በቸርነቱ ፪ሺ፲፫፰ ዘመነ ቅዱስ ማርቆስ የምህረት ዘመንን ያድርግልን።
"ፈሪ ልብ ላላቸው። እነሆ፥ አምላካችሁ በበቀል በእግዚአብሔርም ብድራት ይመጣልና፥ መጥቶም ያድናችኋልና በርቱ፥ አትፍሩ በሉአቸው። ኢሳ ፴፭፥፬
☆☆☆
🌻 ~ በዘመናት የማያረጅ ዘመናትን የሚያስረጃቸው ዘመንን የፈጠረ ሰፍሮ ለሰው የሰጠ ልዑል እግዚአብሔር መጨው ፪ሺ፲፫፰ ዓመተ ምህረትን ባርኮ ለቤተክርስቲያን ይስጥልን፤ የመከራውን ዘመንም በቃ ይበለን፤ የእመአምላክ እናትነቷ ምልጃና ርህራሄ ሊመጣ ካለው መከራ ይጠብቀን ፤አስራት ሀገሯን ኢትዮጵያም በቀደመ ክብሯ ታስብልን አሜን!!!
_ዓመት #እንቁጣጣሽ