11/12/2020
“ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም።” 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4:10
በደል ሁልጊዜ ተበዳዩን ያስቆጣል። በበዳዩም ላይ ፍርድን ያስከትላል። በበዳዩ ላይ የሚደርሰውን ፍርድ የሚወስነው ደግሞ የተበዳዩ ማንነት ነው። ለምሳሌ አንድ ሰው ግለሰብን ሰርቆ ቢያዝና ያው ሰው ደግሞ የመንግስትንና የሕዝብን ሀብት ዘርፎ ቢያዝ ፍርዱ አንድ አይደለም። ምንም እንኳን በሁለቱም ተግባር ተመሳሳይ ሌብነት ቢሆንም፤ አቅምና ጉልበቱ ዝቅተኛ የሆነ ሰው ሲቆጣና ሁሉን ማድረግ የሚችል ፈላጭ ቆራጭ የሆነ መንግስት ሲቆጣ አንድ አይደለም። የተበደለው አካል ማንነት በበዳይ ላይ ሊደርስበት የሚችለውን ፍርድ ይወስናል። የሰው ልጆች በሐጥያታችን የበደልነውና ያሳዘነው የሰማይንና የምድርን ፈጣሪ እግዚአብሔርን ነው። እርሱ ቅዱስ ነው። ብርሀን ነው በብርሀንም ውስጥ ይኖራል። በእርሱ ዘንድ ጨለማ ፈፅሞ የለም። እርሱ ሀጥያትን አያውቅም። ይህንን አምላክ መበደል ከሁሉ የባሰና የጠነከረን ቁጣ ያመጣል። መፅሐፍ ቅዱስ በሐጥያት ስለመጣው ማንነታችን ሲናገር “ከፍጥረታችን የቁጣ ልጆች ነበርን” ይላል ኤፌሶን 2:3። በሐጥያታችን እግዚአብሔር ደስ አልተሰኘም። ይልቁንም ቁጣውን ገለፀ እንጂ። ሐጥያትና የሐጥያት መዘዙ አስከፊ የሆነው ይህንን ታላቅ አምላክ ስለበደልን ነው።
ከእግዚአብሔር ቁጣ ማን ሊያድነን ይችላል? ብለህ ልታስብ ትችላለህ። ለዚህ መልሱ አንድ ብቻ ነው። እርሱም በመስቀል ላይ ስለ ሰው ልጆች ብሎ ራሱን መስዋዕት ያደረገው ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ስራ ለመስራት ብንሞክር መዳን አንችልም። ምክንያቱ ደግሞ የእኛ ስራ የእርሱን ፅድቅ ሊያሟላ ስለማይችል ነው። ልዩ ልዩ ሐይማኖታዊ ስርዓቶችን ብንፈፅምም ደህንነትን ማግኘት አንችልም። ምክንያቱም ሐይማኖት የሰውን የውጫዊ ማንነት ይገራና ያስተካክል ይሆናል እንጂ ፍጥረታችንን ከሐጥያተኝነት ወደ ፃድቅነት ሊለውጥ አይችልም። ታዲያ መፍትሄው ምንድን ነው? መፍትሄው በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ብቻ ነው።
ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የወጣው የአለምን ሁሉ ሐጥያት ተሸክሞ ነው። የእኔን፣ የአንተን፣ የአንቺን፣ የጥቁሩን፣ የነጩን፣ የድሀውን፣ የሐብታሙን፣ የተማረውን፣ ያልተማረውን፣ የሁሉንል ሐጥያት ይዞ በመስቀል ላይ ተሰዋ። ሐጥያት የማያውቀው እርሱ ስለ እኛ ሐጥያት ሆነ። የእግዚአብሔር ቁጣ በመስቀል ላይ ተገለጠበት። ስለ እኛ ሐጥያት እርሱ ደሙን አፈሰሰ። መፅሐፍ ቅዱስ ሲናገር “... እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ።” ይላል ኢሳይያስ 53:6። በእርሱ መስዋዕትነት እኛ ሕይወት አገኘን። የእግዚአብሔርን ቁጣ የሚያበርድ እውነተኛ መስዋዕት ሆነ።
ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ደሙን ሲያፈስ ስለ ሐጥያታችን ዋጋ እየከፈለ ነው። መስዋዕትነቱ እኛን ከሐጥያት ኩነኔ ለማዳን ነው። የእግዚአብሔርን ቁጣ እንዲነድ ያደረገውን ሐጥያት ከእኛ ላይ በደሙ ለመሸፈንና ለማጠብ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ደሙን ሲያፈስ መካከለኛ ሆኖ እኛን ከእግዚአብሔርን ጋር ለማስታረቅ ነው። የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከሐጥያት ሀይል ከሰይጣን እስራት ነፃ የሚያወጣ ብቸኛው የደህንነት መንገድ ነው።
ዛሬ ይህንን የደህንነት ጌታ አዳኝህና ጌታህ አድርገህ ሕይወትህን ብትሰጠው ለዘላልም ለዚህም አለም ዋስትና አለህ። የእግዚአብሔር ልጅ ትሆናልህ። ወዶሀል እንዳትጠፋ የሐጥያትና የሰይጣን ባሪያ ሆነህ ሕይወትህ እንዳያልቅ ኢየሱስ ዋጋውን ከፍሎሀል። ታዲያ ይህንን የእውነት ጌታ ተቀብላችሁ ወደ ሕይወታችሁ እንዲገባ ከፈቀዳችሁ፤ ይህንን ፀሎት ባላችሁበት ፀልዩ።
“የፍጥረት ሁሉ አባት እግዚአብሔር አምላክ ሆይ ከታላቅ ፍቅርህ የተነሳ ልጅህን ኢየሱስ ክርስቶስን ስለ እኔ ሐጥያትና በደል በመስቀል ላይ ደሙን በማፍሰስ መስዋዕት ይሆን ዘንድ አሳልፈህ ስለሰጠሀው አመሰግንሀለሁ። አሁን ደግሞ ኢየሱስ የተሰቀለው፣ የሞተው እንዲሁም ከሞት የተነሳው እኔን ከአምላኬና ከአባቴ ከአንተ ጋር ለማስታረቅ መሆኑ ስለገባኝ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሐጥያቴን ሁሉ ይቅር እንድትለኝ እለምንሀልሁ። ብቸኛው የደህንነት መንገድ ኢየሱስ እንደሆነ ገብቶኛል። ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር መዳን በማንም እንደሌለ አምናለሁ። በልቤ የማምነውን የኢየሱስ ክርስቶስን አዳኝነት በአንደበቴ ‘ብቸኛው አዳኝ ኢየሱስ ነው’ ብዬ እመሰክራለሁ። እግዚአብሔር አምላክ ሆይ ሐጥያቴንና በደሌን ሁሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ስለተሰረዘ አመሰግንሃለሁ። አሁን የአንተ ልጅ ነኝ። ከዚህ በኋላ በእኔ ሕይወት ላይ ሰይጣን፣ አለም፣ ሐጥያት ማናቸውም ገዢ አይሆኑም። የሕይወቴ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ጌታ ሆይ ስላዳንከኝ አመሰግንሃለሁ። አሜን።”
“ፍቅርም እንደዚህ ነው፤ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተስሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም።” 1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4:10