ገዳሜ ተዋህዶ_Gedame tewahido

ገዳሜ ተዋህዶ_Gedame tewahido ቤተክርስቲያን ዘኢትዮጵያ

  ?+።።።።።።።።።።።።።+።።።።።+ገብርኤል ማለት “ እግዚእ ወገብር” - የእግአብሔር አገልጋይ ማለት ነው። ፍጥረታት መፈጠር በጀመሩበት በዕለተ እሑድ እግዚአብሔር መላእክትን ከፈጠራቸው ...
27/04/2026

?
+።።።።።።።።።።።።።+።።።።።+
ገብርኤል ማለት “ እግዚእ ወገብር” - የእግአብሔር አገልጋይ ማለት ነው። ፍጥረታት መፈጠር በጀመሩበት በዕለተ እሑድ እግዚአብሔር መላእክትን ከፈጠራቸው በኋላ ተሰወራቸው መላእክትም “ መኑ ፈጠረነ፡ ማን ፈጠረን ” ሲሉ ዲያብሎስ እኔ ፈጠርኳችሁ ብሎ መላእክት በተረበሹ ጊዜ “ የፈጠረንን አምላካችን እስክናውቅ በያለንበት ጸንተን እንቁም ” ብሎ ያረጋጋቸው መልአክ ነው። በዚህም ምክንያት ጌታ “ በእንተዝ ይደልዎ ከመ ይጹር ዜናሃ ለማርያም ” እንዲል ሥጋዌውን ለድንግል እንዲያበስር አድሎታል።
ከዚህም በኋላ ደጋግ ሰዎችን ለመርዳት የሚወጣ የሚወርድ ሆኗል።
👉ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ በእግዚአብሔር ፊት የሚቆመው ታማኝ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡
👉 በተረዳኢነቱና በአማላጅነቱ በክርስቲያኖች ዘንድ ይወደዳል፡፡
👉 ያዘኑትን ለማጽናናት የምሥራች ለመንገር ከእግዚአብሔር ወደ ምእመናን የሚላክ ይህ ቅዱስ ገብርኤል ነው።

👉ሳጥናኤል ሥላሴን በካደ ጊዜ መላእክትን በቃሉ ያጽናናቸው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

👉ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱና በእግዚአብሔር ፊት የሚቆም ይህ ገብርኤል ነው፡፡

👉በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለሚኖሩ ብርሃን የገለጸና የሰበከ ይህ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

👉የነቢያትን ትንቢት የፈጸመ፤የክርስቶስን ልደት ለድንግል ያበሰረ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

👉ዳንኤልን ከአናብስት ያዳነው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

👉ሠለስቱ ደቂቅን ከእቶን እሳት ያዳነቸው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

👉ወደ ዘካርያስ የተላከ የዮሐንስን ልደት ያበሰረ ይህ ገብርኤል ነው፡፡

👉ወደ ዮሴፍና ወደ ኒቆዲሞስ የተላከ
ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡
👉ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣን ከእቶን እሳት ያዳናቸው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

👉ሰብአ ሰገልን በኮከብ ምልክት የመራቸው
ይህ ገብርኤል ነው፡
@ድንግል ማርያምና ሕፃኑን ክርስቶስን በምድረ በዳ በስደታቸው የመራ ይህ ገብርኤል ነው፡
@የብርሃን ራስ ወርቅ የተቀዳጀ ገብርኤል ነው፡፡
@የአሸናፊና የኃይል መልአክ ገብርኤል ነው፡፡*
@ነበልባላዊ ዖፈ ሰማይ ገብርኤል ነው፡፡

❗️

✝️--የድል አክሊል["🌻-- ዕለተ ትንሣኤ--🌻"]      🙏''''''' እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በዓል በሰላም አደረሳችኹ'''''; !!✝️--ትንሣኤ ማለት [“ተንሥአ”] ካለው የግእዝ ግሥ...
12/04/2026

✝️--የድል አክሊል["🌻-- ዕለተ ትንሣኤ--🌻"]

🙏''''''' እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በዓል በሰላም አደረሳችኹ'''''; !!

✝️--ትንሣኤ ማለት [“ተንሥአ”] ካለው የግእዝ ግሥ የወጣ ሲኾን ትርጉሙም መነሣት ~ መቆም ~ ከአሸናፊነት ጋር መውጣት ማለት ነው።
✝️--ይኽ ዕለት ስሙ ከግብሩ የተስማማለት ቀን ነው ።
✝️--“ትንሣኤ” ማለት መነሣት እንደኾነ °° ክርስቶስም የሞትንና የመቃብርን ሥልጣን ድል አድርጎ ተነሥቶበታልና።
✝️--“ትንሣኤ” ማለት የጨለማው መገፈፍ ማለት እንደኾነ °° ክርስቶስም በዚኽ ዕለት የሰው ልጅን ከሲኦል ጨለማ አውጥቶ ወደ ብርሃን መልሶታልና።
✝️--“ፋሲካ” ማለት መሻገር ማለት እንደኾነ°° ክርስቶስም በዚኽ ዕለት የአዳምን ዘር ከሞት ወደ ሕይወት ፥ ከባርነት ወደ ነፃነት አሻግሮታልና። [፩ኛ ቆሮ ፭÷፯]
✝️--ዕለተ ትንሣኤ፦ የሰው ልጅ ተስፋ መታደሻ ቀን ነው።
✝️--የሞት ኃይል የተሰበረበት ቀን ነው።
✝️--የዲያብሎስ መንግሥት የፈረሰበት ቀን ነው።
✝️--የሰው ልጅ ነፃነት ቀን ነው።
✝️--የመቃብር መክፈቻ ቀን ነው።
✝️--የገነት ደጅ መከፈቻ ቀን ነው።
✝️--የሐዘን መለወጫ ቀን ነው።
✝️--የሰላም አዋጅ ቀን ነው።
✝️--የትንቢትና የምሳሌ ኹሉ ፍጻሜ ቀን ነው።
✝️--የሰላምና የዕርቅ ቀን ነው።
✝️--የዘለዓለም ሕይወት ዋስትና የተረጋገጠበት ቀን ነው።
✝️--የነፍሳት ከሲኦል መውጫ ቀን ነው።
✝️--የሰውና የመላእክት አንድነት የታወጀበት ቀን ነው።
✝️--የሕይወት እስትንፋስ የታደሰበት ቀን ነው።

✝️--በዚኽ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምንና ልጆቹን ከዲያብሎስ ቀንበር ነፃ ያወጣ ዘንድ፥ በከርሠ መቃብር ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት ከቆየ በኋላ በታላቅ ግርማና ሥልጣን የተነሣበት ዕለት ነው።
✝️--ምንም እንኳ አይሁድ መቃብሩን በታላቅ ድንጋይ ቢገጥሙት ፥ በማኅተም ቢያትሙት፥ በጭፍሮችም ቢያስጠብቁት ፥ጌታ ግን ማኅተመ መቃብሩን ሳይለውጥ [ሳይሰብር ] እንደወጣ በቅዱሳት መጻሕፍት ተመስክሯል።
✝️--በዚኽ ዕለት የተከናወኑ ታላላቅ ተአምራቶችና ድርጊቶች ለ፲፫ ይመደባሉ። እነርሱም የሚከተሉት ናቸው፦[ ]
✝️--፩ኛ፦ መቃብርን በሥልጣኑ መክፈቱ [ኃይለ ትንሣኤ]።
✝️--፪ኛ፦ ማኅተመ መቃብሩ ሳይለወጥ መነሣቱ [መለኮታዊ ተአምር]።
✝️--፫ኛ፦ መልአኩ ወርዶ ድንጋዩን ማንከባለሉ [ለአበጋዞቹ ድንጋጤ `` ለመላእክት ደስታ]።
✝️--፬ኛ፦ የመቃብር ጠባቂዎች እንደ በድን መውደቃቸው [የአይሁድ ሽንፈት]።
✝️--፭ኛ፦ በፍታውና መጠምጠሚያው በሥርዓት ተቀምጦ መገኘቱ [ሥርዓተ ትንሣኤ ] ።
✝️--፮ኛ፦ ለመግደላዊት ማርያም በገነት አትክልተኛ አምሳል መታየቱ ።
✝️--፯ኛ፦ ለቅዱሳት አንስት “ደስ ይበላችኹ” ብሎ የምስራች ማብሰሩ።
✝️-- ፰ኛ፦ ለጴጥሮስና ለዮሐንስ መቃብሩ ባዶ መሆኑ መታየቱ።
✝️--፱ኛ፦ ለኤማሁስ መንገደኞች በመንገድ ተገልጦ መጽሐፍትን መተርጎሙ።
✝️--፲ኛ፦ በዝግ ደጅ ገብቶ ለሐዋርያት “ሰላም ለእናንተ ይኹን” ማለቱ።
✝️--፲፩ኛ፦ በቶማስ እጅ ጎኑንና እጁን በማስዳሰስ ጥርጣሬን ማጥፋቱ።
✝️--፲፪ኛ፦ የገነት ደጅ መከፈቱን ለዓለም ማብሰሩ።
✝️--፲፫ኛ፦ ለደቀ መዛሙርቱ በባሕረ ጥብርያዶስ ተገልጦ ቁርስን መመገቡ።

✝️--በዚኽም ዕለት ክርስቶስ የሞትን መውጊያ ሰብሮ ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቷል። ✝️የሕይወት መንገድን ከፍቶልናል።
✝️-- የጠፋውን በግ አዳምን ወደ ቀደመ ቦታው መልሶታል።
✝️--ይኽችውም [ ዕለተ ትንሣኤ] በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት ታላቅ የምስራች የሚነገርባት ናት፦ [< >]
✝️-- ፩ኛ፦ ሌሊቱን ሙሉ ማኅሌት ሲቆም ያድራል።
✝️--፪ኛ፦ ካህናቱ ነጭ ልብስ ለብሰው “ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን” እያሉ ያበሥራሉ።
✝️--፫ኛ፦ “በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን” እየተባለ የጌታ አሸናፊነት ይነገራል።
✝️--፬ኛ፦ “አሰሮ ለሰይጣን” እየተባለ የጠላት ውድቀት ይበሰራል።
✝️--፭ኛ፦ “አጋእዞ ለአዳም” እየተባለ የሰው ልጅ ነፃነት ይውጃል።
✝️--፮ኛ፦ “ሰላም እምይእዜሰ ኮነ ፍሥሐ ወሰላም” እየተባለ የዓለም ሰላም ይታወጃል።
✝️--፯ኛ፦ የትንሣኤው ብርሃን በሻማና በፋኖስ ይገለጻል።
✝️--፰ኛ፦ የታሰሩት የሚፈቱበት~ የታረዙት የሚለብሱበት የፍቅር ማዕድ ይዘረጋል።
✝️--፱፦ ጥቁር ልብስ በነጭ ይተካል።
✝️--፲፦ ምዕመናን “በእውነት ተነሥቷል” በሚል ሰላምታ ይለዋወጣሉ።

✝️--በዚኹ ዕለት ዲያቆኑ ነጭ ለብሶ፣ መስቀል ይዞ~ በደስታ ቃጭል እያቃጨለ " ለአዳም ትንሣኤው ሰላም ኾነ] እያለ ቤተ ክርስቲያኑን መዞሩ፣ መላእክት የጌታን ትንሣኤ ለዓለም ያበሰሩበት ምሳሌ ነው።

✝️--ማክፈል፦ እመቤታችን

 ~~~~~~~ትንሣኤ የሚለውን ቃል በጥልቀት ስንመረምረው፣ ከቋንቋ ጥናት ባለፈ የሰው ልጅ ለሕይወት፣ ለሞትና ለተስፋ ያለውን አመለካከት የሚገልጽ ታላቅ ጽንሰ-ሐሳብ ነው። ብዙውን ጊዜ በከፍተ...
12/04/2026


~~~~~~~

ትንሣኤ የሚለውን ቃል በጥልቀት ስንመረምረው፣ ከቋንቋ ጥናት ባለፈ የሰው ልጅ ለሕይወት፣ ለሞትና ለተስፋ ያለውን አመለካከት የሚገልጽ ታላቅ ጽንሰ-ሐሳብ ነው። ብዙውን ጊዜ በከፍተኛ ትምህርት የምናውቀው ሳይንስ ስላለ ከሱ ጋር በማያያዝ የትንሣኤን ትርጕም ለመግለጽ እንሞክራለን። ይህንን ቃል በሦስት ዋና ዋና መነጽሮች ማለትም በቋንቋ (Etymology)፣ በታሪክ ፍልስፍና እና በማኅበራዊ ሳይንስ (ሳይኮሎጂና አንትሮፖሎጂ) በዝርዝር እንተንትነው።
​1. በመጀመሪያ በቋንቋ ትንታኔ (Etymological Analysis)

፩.​ግእዝ: "ትንሣኤ" የሚለው ቃል የመጣው "ተንሥአ" (ተነሣ) ከሚለው የግእዝ ስርወ ግስ ነው። ትርጉሙም መነሣት፣ ከአንቀልፋት መንቃት፣ ወይም ካለበት ዝቅታ ወደ ላቀ ደረጃ መሸጋገር ማለት ነው። በግእዝ ሥነ-ጽሑፍ "ትንሳኤ" ሲባል የነፍስና የሥጋ ዳግም መዋሐድ ብቻ ሳይሆን፣ አዲስ ሕይወት መጀመርንም ያመለክታል።
፪.​ግሪክ (Koine Greek): በአዲስ ኪዳን "አናስታሲስ" (ἀνάστασις) ይባላል። Ana (እንደገና/ወደ ላይ) እና stasis (መቆም) ከሚሉ ቃላት የተዋቀረ ነው። ትርጕሙም "እንደገና መቆም" ወይም "ዳግም መቆም" ማለት ነው። ይህም ሞት እንደ መውደቅ ተቆጥሮ፣ ትንሣኤ ደግሞ ያንን ውድቀት ድል አድርጎ ቀጥ ብሎ መቆምን ያሳያል።
፫.​ዕብራይስጥ: "ተቁማህ" (תקומה) ወይም "ትሒያት ሃሜቲም" (תחיית המתים) ይባላል። ትርጉሙም "ሙታንን ሕያው ማድረግ" ማለት ነው። ይህም አምላካዊ በሆነ ኃይል ሕይወት አልባ የሆነውን ነገር ወደ ሕያውነት የመመለስ ተግባር ላይ ያተኩራል።
​2. የታሪክ ፍልስፍና (Philosophy of History)
​በታሪክ ፍልስፍና እይታ፣ ትንሣኤ የ"ታሪክ መስመራዊ ጉዞ" (Linear History) ማሳያ ነው።
# ​ክበባዊ (Cyclical) vs መስመራዊ (Linear): ጥንታዊ ግሪኮችና ሕንዳውያን ታሪክ እንደ ክበብ ይሽከረከራል (እንደገና መወለድ/Reincarnation) ብለው ያምኑ ነበር። ትንሣኤ ግን ታሪክ መጀመሪያና መጨረሻ እንዳለው፣ በመጨረሻም የሞትና የክፋት ድል ተመትቶ የታሪክ ግብ (Telos) እንደሚሆን ያስተምራል።
# ​የፍትሕ ፍልስፍና: ትንሣኤ በታሪክ ውስጥ ለተበደሉ፣ በግፍ ለሞቱና ዋጋ ላላገኙ የሰው ልጆች "የመጨረሻ ፍትሕ" (Ultimate Justice) የሚሰጥበት የታሪክ ማጠቃለያ ተደርጎ ይወሰዳል።
​3. ከአንትሮፖሎጂ አንጻር (Anthropological Perspective)
​አንትሮፖሎጂ ትንሣኤን የሰው ልጅ በአንትሮፖሎጂ መነጽር ስናየው ትንሣኤን "ባሕላዊ ማንነት" እና "ከአካባቢው ጋር ያለው ግንኙነት" መግለጫ አድርጎ ያየዋል። ልክ ነው አይደለም ሌላ ጥያቄ ነው። አንትሮፖሎጂስቶች የሰውን ልጅ ከትንሣኤ ጋር ሲያዛምዱት ግን ሳይንሱን በዚህ መንገድ አብራርተውታል። አንትሮፖሎጂን ያነሣሁት"ሰው" አንትሮፖስ" የሚል ቃል ከቃሉ ተፈልቅቆ ስለሚወጣ ነው"ሰው ካለ(አጥብቅ) ትንሳኤ አለ ስለዚህ ማዛመድ ይኖርብናል።
# ​የሰው ልጅ ተፈጥሮ: ሰው ሥጋ ብቻ ሳይሆን መንፈሳዊ አካልም እንዳለውና ይህ አካል ደግሞ ከጠፈርና ከምድር ጋር የተቆራኘ መሆኑን አንትሮፖሎጂ ያሳያል።
# ​የማኅበረሰብ ተስፋ: በብዙ ባህሎች ውስጥ የትንሳኤ እምነት የሞቱ አባቶችን የማክበርና "ሞት መጨረሻ አይደለም" የሚል ማኅበራዊ ትስስር የመፍጠሪያ መንገድ ነው። ትንሣኤ ሰውን ከምድራዊ ውሱንነት አውጥቶ ከዘለዓለማዊነት ጋር የሚያገናኝ እንደ አትሮፖሎጂ "ባህላዊ ድልድይ" ነው ይለዋል።
​4. ከሳይኮሎጂ አንጻር (Psychological Perspective)
​በሳይኮሎጂ እይታ፣ ትንሣኤ በሰው አእምሮ ውስጥ ያለውን "የለውጥና የዕድገት ፍላጎት" (Transformation) ይወክላል።
#አርኪታይፓል (Archetypal) እይታ: ታዋቂው ሳይኮሎጂስት ካርል ዩንግ እንደሚለው፣ ትንሣኤ በሰው ልጅ የጋራ አእምሮ (Collective Unconscious) ውስጥ ያለ ምልክት ነው። ይህም "የድሮውን ማንነት ገድሎ አዲስና የተሻለ ማንነትን የመላበስ" (Self-actualization) ሂደት ተምሳሌት ነው ይለናል።
#የጭንቀት ድል: ሞት የሰው ልጅ ትልቁ ስጋት (Existential Anxiety) ነው ምክንያቱም የሰው ልጅ ተወለደ÷ አደገ÷ ኖረ ÷ ሞተ ከዚያስ የሚል መሠረታዊ ጥያቄ አለ የህልውና ጥያቄ። ትንሣኤ ይህንን ስጋት በማስወገድ፣ አእምሮአዊ ሰላምና ትርጉም ያለው ሕይወት ለመምራት የሚረዳ "ሳይኮሎጂካዊ የመቋቋሚያ ዘዴ" (Coping Mechanism) ነው ምክንያቱም ቅዱስ መጽሐፋችን እንደሚነግረን "ሞት መወጊያህ የት አለ" ይለናል ሞት ተሸንፏል ሞት ከተሸነፈ የሰው ልጅ ፈርሶ በስብሶ አይቀረም ምክንያቱም ሞት ተሸንፏል።
#​ተስፋ (Hope): በሳይኮሎጂ "ተስፋ" ለሰው ልጅ ህልውና ወሳኝ ነው። ትንሣኤ እጅግ በጨለመና ተስፋ በቆረጠ ሁኔታ ውስጥ "ብርሃን አለ" ወድቆ መነሣት አለ "አፈር ሆኖ÷በስብሶ አለመቅረት አለ"የሚል አእምሮአዊ ጥንካሬን ይሰጣል።
​ትንሣኤ በቋንቋ ደረጃ መነሣት ቢሆንም፣ በፍልስፍናው የታሪክ ግብ፣ በአንትሮፖሎጂው የሰው ልጅ ክብር፣ በሳይኮሎጂው ደግሞ የአእምሮ ድልና ተስፋ ነው። ይህ ጽንሰ-ሐሳብ የሰው ልጅ እራሱን ከቁሳዊው ዓለም በላይ ከፍ አድርጎ እንዲያይ የሚያደርግ የታላቅነት ማረጋገጫ ነው።

ክፍል÷፪

የታሪክ እና የትንሣኤው ክንውን ትንታኔ በማቴዎስ ወንጌል የተጻፈውን የትንሣኤውን ወንጌል በቁጥር በቁጥር ያለውን ሐሳብ ለማብራራት እንሞክራለን። ይሄን ከማንባችሁ በፊት ግን ማቴዎስ ምእራፍ 28 ሙሉውን ብታነቡት ካነበባችሁት ጥሩ እና ከዛ በኋላ ማብራሪያውን እንረዳለን።
(ቁጥር 1-10)
#​ቁጥር 1 "በሰንበትም መጨረሻ... መግደላዊት ማርያምና ሁለተኛይቱ ማርያም መቃብሩን ሊያዩ መጡ።" ትንሣኤው በታሪክ የተረጋገጠው በመጀመሪያ ሴቶች ምስክሮች በመሆናቸው ነው። በወቅቱ በነበረው የአይሁድ ባሕል የሴቶች ምስክርነት እንደ ትልቅ ነገር ባይቆጠርም፣ ወንጌላዊው ይህንን መጥቀሱ የታሪኩን እውነተኝነት ያሳያል።
#​ቁጥር 2-4 (የመላእክት መታየት): "ታላቅ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ፤ የጌታ መልአክ ከሰማይ ወርዶ ነበርና ይለናል።" እዚህ ጋር የመልአኩ ሚና መቃብሩን ከፍቶ ክርስቶስ እንዲወጣ ለማድረግ ሳይሆን (ክርስቶስ አስቀድሞ በዝግ መቃብር ተነሥቷል)፣ መቃብሩ ባዶ መሆኑን ለሰዎች ለማሳየት ነው። መላእክት በጌታ ልደት፣ በፈተናው እና በጌቴሴማኒ እንደነበሩ ሁሉ በትንሣኤውም የሰማያዊው ዓለም ምስክሮች ናቸው።
#​ቁጥር 5-7 (የመዳን ብሥራት): መልአኩ "እናንተስ አትፍሩ... ተነሥቷል" አላቸው። ይህ የድል አዋጅ ነው። ሞት መሸነፉን እና የሰው ልጅ ከኃጢአት ባርነት ነፃ መውጣቱን የሚያበስር የመዳን መጀመሪያ ነው። ሙሉው ምዕራፍ በሊቃወንት ትምህርት በሚለው ርእስ ላይ ይደመደማል ።
​2. ትንሳኤው በብሉይና በሐዲስ ኪዳን አረዳድ(Typology)

፩.በብሉይ ኪዳን

#​የክርስቶስ ትንሳኤ ድንገተኛ ክስተት ሳይሆን በብሉይ ኪዳን የተተነበየና በሐዲስ ኪዳን የተፈጸመ ነው።
# ​ትንቢተ ዮናስ: ዮናስ በዓሣ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት መቆየቱ የክርስቶስ መቃብርና ትንሣኤ ጥላ ነበር ብሎ ማቴዎስ ዘግቦልናል።(ማቴ 12፡40)።
#​መዝሙር 16፡10: "ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፥ ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትተወውም።" ይህ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት የተናገረው የትንሳኤው ቀጥተኛ ትንቢት ነው።

፪.በሐዲስ ኪዳን።

# ​1ኛ ቆሮንቶስ 15፡20: "አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተነሥቷል።" ትንሣኤው ለሰው ልጆች ሁሉ ትንሳኤ መንገድ የከፈተ መሆኑን ያረጋግጣል።

፫.በሊቃውንት ትምህርት አረዳድ

​የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ትንሣኤውን በሚከተሉት 10 ነጥቦች ያጸኑታል፡
: መቃብሩ ባዶ መሆኑን የአይሁድ ባለሥልጣናት እንኳ አልካዱም፤ ይልቁንም "ደቀ መዛሙርቱ ሰረቁት" የሚል ደካማ ምክንያት ነው የሰጡት (ማቴ 28÷13)።
#የተለወጡት ደቀ መዛሙርት: በፍርሃት ተደብቀው የነበሩት ደቀ መዛሙርት በድንገት ስለ ትንሣኤው ለመመስከር እስከ ሞት መድረሳቸው ትንሣኤው እውነት መሆኑን ያሳያል።
#የመግነዙ አቀማመጥ: በዮሐንስ ወንጌል እንደተጠቀሰው መግነዙ ተጠቅልሎ መቀመጡ ሌባ እንዳልሰረቀው (ሌባ መግነዝ አይፈታም)፣ ይልቁንም በሥልጣኑ እንደተነሣ ያሳያል። ተመልከቱ ዛሬ ሁሉ በአይሁድ ባሕል ክርስቶስ አልተነሣም ሌቦች ከመቃብር ሰረቁት እንጂ ይላሉ። ማቴዎስም ተንኮላቸውን ገልጦ ጽፏል። መቃብሩን ሲጠብቁ ያደሩ ጭፍራዎችን ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት ሠረቁት በሉ ብለው እንዳባበላቸው። ስለዚህ ፍቁረ እግዚእ ዮሐንስ ይሄን ክፋታቸውን ሲገልጥባቸው መግነዙ ተጠቅልሎ መቀመጡ ሌባ እንዳልወሰደው ማስረጃ ነው። ሌባ ቢወስደው መግነዙን አይፈታውም ነበር ብሎ ለአይሁድ መልስ ይመልስላቸዋል።
​ #የተቃዋሚዎች ዝምታ: አይሁድ የትንሣኤውን ወሬ ለማቆም የክርስቶስን ሎቱ ስብሐት አስከሬን ማቅረብ ይችሉ ነበር፤ ነገር ግን አስከሬኑ ባለመኖሩ ውሸት መፍጠር መረጡ።
#የሰንበት መቀየር: ከአባቶች ጀምሮ የነበረው የቅዳሜ አከባበር ክርስቶስ በተነሣበት እሑድ መተካቱ የክስተቱን ታላቅነት ያሳያል።
#የተለያዩ መገለጦች: ክርስቶስ ለአንድ ሰው ብቻ ሳይሆን በአንድ ጊዜ ከ500 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች ታይቷል (1 ቆሮ 15፡6) ምርጥ እቃ የተባለው ቅዱስ ጳውሎስ እንደዘገበልን ።
#የቤተ ክርስቲያን መመሥረት: ያለ ትንሣኤ ቤተ ክርስቲያን ልትመሠረት አትችልም ነበር፤ የቤተ ክርስቲያን መኖር ራሱ የትንሣኤው ውጤት ነው።
#​ትንቢታዊ ንግርቶች: ትንሣኤው በኦሪት፣ በነቢያትና በመዝሙር የተነገሩትን ከመቶ በላይ ትንቢቶች ፈጽሟል።
#የሐዋርያት ሰማዕትነት: ሰዎች ለሚያውቁት ውሸት ሕይወታቸውን አይሰጡም ፤ በእሳት እንደ ንፍሮ አይቀቀሉም ነበር ÷ በመጋዝ እንደ ሽንርኩት አይላጡም ነበር ክርስቶስ ባይነሣ ለማያውቁት እውነት ይህን ያህል መሥዋዕትነት ለምን ይከፍላሉ? ነገርግን ሞት በክርስቶስ ትንሳኤ ድል ሲደረግ ስለተመለከቱ ሞትን ናቁት ÷ አቃለሉት ÷ አዋረዱት ቶሎ ወደ ትንሣኤው ጌታ ወደ ክርሰቶስ መሄድ ይሻለናል እያሉ ወደ ክርስቶስ በሰማዕትነት መንገድ ጨክነው ተራመዱ። በዚህም ምክንያት ሐዋርያት ያዩትን እውነት ለመመስከር አንገታቸውን ለሰይፍ ለሰይፍ ሥጋቸውን ለስለት ሰጡ። ውስተ ኵሉ ምድር ወጽአ ነገሮሙ ÷ ወእስከ አጽናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ" አላቸው ባለ በገናው ቅዱስ ዳዊት (መዝ 18)። ያዩትን እውነት ሊመሰክሩ እስከ ዓለም ዳርቻ ወጡ። ትምህርታቸውም እስከ ዓለም ዳርቻ ደረሰ አለ።
#​የጌታ ትእዛዝ (ቁጥር ማቴ 28÷19-20): "ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው" የሚለው ታላቅ ተልእኮ ክርስቶስ በሕይወት መኖሩንና ከእኛ ጋር እስከ ዓለም ፍጻሜ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው። እነዚህ የጠቀስናቸው ሐሳቦች ሁሉ የክርሰቶስ ትንሣኤ ማስረጃዎች ናቸው።

"ንህነሰ ነአምን ሕማሞ ወትንሣኤሁ ለክርስቶስ በአማን"

​የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 28 ትንሣኤውን የሚገልጸው እንደ ተራ ታሪክ ሳይሆን፣ ዓለምን ኹሉ የሚለውጥ ፣ ሞትን ድል የነሣና ለሰው ልጅ የዘላለም ሕይወት የተሰጠበት ታላቅ የድል ምዕራፍ አድርጎ ነው። ክርስቶስ ተነሥቷል ሞትም ተሸንፏል!

✨መልካም በዓለ ትንሣኤ✨
--------------------------
©ገዳሜተዋህዶ

 ⨳⨳⨳⨳⨳⨳⨳⨳በጲላጦስ ዘመን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት፤ ትንቢቱም ይፈጸም ዘንድ መከራን ተቀበለ፤ ጲላጦስ በ፫ ሰዓት ይሰቅል ዘንድ ሲፈርድ...
10/04/2026


⨳⨳⨳⨳⨳⨳⨳⨳

በጲላጦስ ዘመን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት፤ ትንቢቱም ይፈጸም ዘንድ መከራን ተቀበለ፤ ጲላጦስ በ፫ ሰዓት ይሰቅል ዘንድ ሲፈርድበትም፤ ‹‹መስቀሉንም ተሸክሞ በዕብራይስጥ ጎልጎታ ወደ ተባለው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ወጣ›› (ዮሐ.፲፱፥፲፯) የራስ ቅል ስፍራ ቀራንዮ-ጎልጎታ አዳም ዐጽም የተቀበረበት ቦታ ነበር፡፡ በዚያም የአዳም መቃብር የሆነች ዋሻ አለች፤ የመስቀሉንም እንጨት በዚያ በምድር መካከል አይሁዶች ተከሉት፡፡ የአዳም አጽም ቀድሞ ከአዳም ትውልዶች ሲተላለፍ ከኖኅ ደርሷል፤ ኖኅም ወደ መርከብ እንደታቦት አስገብቶት በኋላ መልከጼዴቅ ቀብሮታል፡፡ ጌታችንም ከአዳም የራስ ቅል በላይ ሊያድነው መስቀል ተሸከሞ ተንገላታ፤ አይሁዶችም የቀራንዮን ዳገት እየገረፉ ከወደ ጫፍ አደረሱት፤ሁለቱንም እንጨት አመሳቅለው ዐይኖቹ እያዩ እጆቹንና እግሮቹን ቸነከሩት፤ በዕለተ ዐርብ ቀትር ፮ ሰዓት ላይም ተሰቀለ፡፡

ጌታችን የተሰቀለበት ሰዓት ፀሐይ በሰማይ መካከል በሆነ ጊዜ የጥላ መታየት በሚጠፋበት፤ ወደ ሰው ተረከዝም በሚገባበት ነበር፡፤ ከ፮ ሰዓት ጀምሮ እስከ ፱ ምድር ጨለመች፤ ፀሐይ፤ጨረቃ፤ከዋክብት ብርሃናቸውን ከለከሉ፤ ምክንያቱም የፈጣሪያቸውን ዕርቃኑን ይሸፍኑ ዘንድ ነበር፤ ‹‹ቀትርም በሆነ ጊዜ ፀሐይ ጨለመ፤ምድርም ሁሉ እስከ ፱ ሰዓት ድረስ ጨለማ ሆነ›› ማር.፲፭፥፴፫፡፡

በ፱ ሰዓት በቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ ስለ ጌታችን በሰማይ ፫ት በምድር ፬ት ተአምራትን ሲያደርጉ አይቶ በእውነት አምላክ እንደሆነ አመነ፤ ‹‹አቤቱ በመንግሥት በመጣህ ጊዜ አስበኝ›› ባለ ጊዜ በግራ የተሰቀለው ዳክርስ ግን ‹‹እስቲ አምላክ ከሆነ እራሱን ያድን›› ብሎ ተዘባበተ፡፡ ፍያታዊ ዘየማን ግን ‹‹እኛስ በበደላችን ነው የተሰቀልን፤ እርሱ ግን ምንም ሳይበድል ነው፤ እንዴት በአምላክ ላይ ክፉ ነገርን ትናገራለህ›› ብሎ ገሰጸው ፤ፍያታዊ ዘየማንም ጌታችን በጌትነት መንበረ ጸባዖት(መንግሥት) ሆኖ ታየው፤እርሱንም አይቶ ‹‹ተዘከረኒ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ›› ቢለው ጌታችን ‹‹ዮም ትሄሉ ምስሌየ ውስተ ገነት›› ብሎ ደመ ማኅተሙን ሰጥቶታል፤ በኋላ ገነት ሲገባም መልአኩ አንተ ማነህ፤ አዳም ነህ፤ አብርሃም ወይንስ ይስሐቅ? እያለ ጠይቆታል፡፡ መልአኩ ሳያውቅ የጠየቀ ሆኖ አይደለም፤እንኳን በመጨረሻ የጸደቀ ፍያታዊ ቀርቶ በዘመናቸው የኖሩ ጻድቃንን ያውቃል፤ አዳምን ፤አብርሃምን፤ይስሐቅን ሳያውቅ ቀርቶም አይደለም፡፡ ነገር ግን ሊቃውንት ሲተረጉሙት ‹‹አዳም ነህ›› ማለቱ የአዳምን ያህል ሥራ አለህን? አብርሃም ነህ ሲለው ደግሞ የአብርሃምን ያህል ሥራ አለህን? ለማለት ነው፡፡ ‹‹በጌታችን ኢየሱስ መስቀል አጠገብም እናቱ፤ የእናቱም እኅት፤ የቀለዮጳም ሚስት ማርያም፤መግደላዊትም ማርያም ቆመው ነበር›› (ዮሐ.፲፱፥፳፭) ‹‹እነርሱም ማርያም መግደላዊት፤ የታናሹ ያዕቆብ እና የዮሳ እናት ማርያም፤ የዘብዴዎስም የልጆቹ እናት ሰሎሜም ነበሩ›› (ማር.፲፭፥፵)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከተናገራቸው የአደራ ቃላት አንዱ እመቤታችን ለቅዱስ ዮሐንስ መሰጠቷ ነው፤ ለወዳጁ ዮሐንስ ከስጦታ ሁሉ ስጦታ የሆነች እናቱን እናት ትሁንህ ብሎ ሰጠው፤‹‹እነኋት እናትህ፤ እነሆ ልጅሽ›› (ዮሐ.፲፱፥፳፮)፡፡ በኋላ ወደ ቤቱ ወስዷት ፲፭ ዓመት ኖራለች፤ በዚህም የዮሐንስ ቤት በአቢዳራ ቤት ተመስላለች፤እመቤታችንም የሚያጽናናትን ወዳጁ ዮሐንስን ሰጥቷታል፡፡ የእመቤታችን ለዮሐንስ መሰጠት ቀድሞ በሙሴ አንጻር ጽላቷ ለሕዝቡ ሁሉ እንደተሰጠች፤በዮሐንስ አንጻርም እመቤታችን ለሁላችን ለምእመናን ተሰጥታናለች፡፡

፱ ሰዓት በሆነ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ፤አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ›› ብሎ በታላቅ ቃል ተናገረ፤(ማር.፲፭፥፴፬)፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት ‹‹አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ፤›› የሚለውን ድምጽ የሰሙ ኤልያስን ይጣራል እያሉ አሙት፤ ክህደትንም ተናገሩ፤ ያንጊዜ አንዱ ወታደር ሮጦ ሆምጣጤ የመላበት ዕቃ ተቀምጦ ነበርና በሰፍነግ መልቶ በሂሶጽም አድርጎ በአፉ ውስጥ ጨመረለት፡፡

በመስቀል ላይ ሳለ ጌታችን ኢየሱስም በታላቅ ድምፅ ሁሉ ተፈጸመ አለ፤ (ማር. ፲፭፥፴፯)፤ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በፈቃዱ ለየ፡፡ አይሁድም እኒህ ሰዎች እንደተሰቀሉ አይደሩ፤ ምክንያቱም ቀጣዩ ቀን ሰንበት ነውና ጭናቸውን ሰብረው ያወርዷቸው ዘንድ ጲላጦስን ጠየቁት፤ እርሱም ፈቀደላቸው፡፡ የሁለቱ ወንበዴዎች፤ ፈያታይ ዘየማንንና ፈያታይ ዘጸጋምን አብረው አወረዷቸው፤ ከጌታችን ዘንድ ቢቀርቡ ፈጽሞ ሞቶ አገኙት፤ በዚህም ጭኑን ሳይሰብሩት ቀሩ፡፡ ሌላው ግን የተመሰለው ምሳሌ ፍጻሜ ሲያገኝ ነው፤ የፋሲካውን በግ ‹‹አጥንቱን ከእርሱ አትስበሩ›› የተባለው አሁን ተፈጸመ፤(በዘፀ.፲፪፥፲)፡፡ ከጭፍሮቹም አንዱ ቀኝ ጎኑን በጦር ወጋው እንዲል ከወታደሮቹ አንዱ የሆነው ለንጊኖስ የጌታችንን ጎን ቢወጋው ትኩስ ደምና ቀዝቃዛ ውኃ ፈሷል፡፡ ለንጊኖስ ጥንተ ታሪኩ አንድ ዐይኑ የጠፋ ሲሆን ጌታችን በተሰቀለበት ጊዜ ወደ ጫካ ሸሽቶ ርቆ ነበር፤ ምክንያቱም ከዚህ ሰው ሞት አልተባበርም በማለት ነው፡፡ አመሻሹ ላይ የአይሁድ አለቆች ሲመለሱ ከመንገድ አገኘቱ፤ስለምን ከመሢሑ ሞት አልተባበርክም አሉት? እርሱም ምንም ስላላገኘሁበት አላቸው፡፡ ከዚያም በኋላ እንደሕጋቸው እንደሚቀጡት ቢነግሩት እየሮጠ ሔዶ የጌታችንን ጎን ሲወጋው ደሙ በዐይኑ ላይ ፈሰሰ፤ ያን ጊዜ ዐይኑ በራለት፤ከጌታችን ጎን የፈሰሰው ደም እንደ ለ ቅርጽ ሆኖ በሁለት ወገን ደምና ውኃ ሆነ፡፡ ከጌታችንም የፈሰሰውን ትኩስ ደም መላእክት በጽዋ ቀድተው በዓለም ላይ ረጩት፤ ይህ መሠረት ሆኖ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታነጸው የጌታችን ደም የነጠበበት ነው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹አሁንም በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ›› ያለው (ሐዋ.፳፥፳፰)፡፡ ከጌታ ጎን የፈሰሰው ውኃ ደግሞ ምእመናን የልጅነት ጥምቀትን ስንጠመቅ ውኃውን ካህኑ ሲባርከው ማየ ገቦ ይሆናል፡፡

ቅዳሜ ከቀድሞው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው ቅዳሜ ትባላለች፤ ይህ ቅዳሜ ጌታችን ሥጋው በመቃብር የዋለበት በመሆኑ እኛም እንደ ሐዋርያት የትንሣኤውን ብርሃን ሳናይ እህል አንቀምስም በማለት በጾም ስለምናሳልፈው ነው፡፡ ቄጠማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤው ሌሊት በራሳቸው ላይ ያሰሩታል፤ የቄጠማው አመጣጥና ምሥጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፤ ምድር በጥፋት ውኃ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሠረችው ቄጠማ ይዛ በመግባት ነው፡፡ ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ኃጢአት ጠፋ፤ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነፃነት ተሰበከና ታወጀ በማለት ካህናቱ ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበስሩበታል፡፡

በዚህች ቅድስት ቅዳሜ፤ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ፤ በዚህች ዕለት ከሥራው ሁሉ ያረፈባት ዕለት ናት፡፡ ጌታችን የተቀበረበትም ስፍራ ለተሰቀለበት ቦታ አቅራቢያ ነበር፤ ዮሴፍ ከኒቆዲሞስ ጋር ሆኖ ጌታችንን እንደፍጡር በሐዘንና በልቅሶ ሲገንዙት የጌታችን ዐይኖች ተገለጡ ‹‹እንደፍጡር ትገንዙኛላችሁን? በሉ እንዲህ እያላችሁ ገንዙኝ፤ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ ቅዱስ ኃያል፤ ቅዱስ ሕያው›› አላቸው፡፡



#ስቅለት
#ፋስካ

#በዓል
#ስግደት
#ኢትዮጵያ

 ==========ጸሎተ ሐሙስ ጌታችን አምላካችን ምሥጢረ ቊርባንን ከምሥጢረ ጸሎት ጋር አዋሕዶ የገለጠበት ዕለት ነው፡፡ይህ ዕለት ቅድመ ዓለም ለፍጥረታት ሁሉ ምግበ ሥጋን የፈጠረ ጌታ ለሰው ...
08/04/2026


==========

ጸሎተ ሐሙስ ጌታችን አምላካችን ምሥጢረ ቊርባንን ከምሥጢረ ጸሎት ጋር አዋሕዶ የገለጠበት ዕለት ነው፡፡

ይህ ዕለት ቅድመ ዓለም ለፍጥረታት ሁሉ ምግበ ሥጋን የፈጠረ ጌታ ለሰው ልጆችም ሁሉ ምግበ ነፍስን የሠራበት፣ራሱን ማዕድ አድርጎ ብሉኝ ትድናላችሁ ያለበትና ይህንን ምግብ ለመቀበል ቅድሚያ መደረግ ያለበትን ሥርዓተ ጸሎት ያስተማረበት ዕለት ነው፡፡

በዚህ ዕለት ጌታችን ትሕትናን ለማስተማር የሐዋርያትን እግር ያጠበበት ዕለት በመሆኑም ሕጽበተ እግር የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡

እርሱ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የደቀ መዛሙርቱን እግር ካጠበ በኋላ ‹‹እናንተ መምህራችን፣ ጌታችን ትሉኛላችሁ፤ መልካም ትላላችሁ፡፡ እኔ ጌታችሁ መምህራችሁ ስሆን ዝቅ ብዬ እግራችሁን ካጠብኋችሁ እናንተም ዝቅ ብላችሁ የወንድሞቻችሁን እግር ልታጥቡ ይገባችኋል፡፡ ምሳሌ ሆኛችኋለሁና፤›› በማለት የትሕትና ሥርዓት ሠርቶ እነርሱም በሥራ እንዲገልጡት አዝዞአቸዋል (ዮሐ. ፲፫፥፲፭)፡፡

ጌታችን እኛ መከራና ፈተና በገጠመን ጊዜ ተግትን እንድንጸልይ ለማስተማር እንዲሁም ኅብስቱን ለመባረክ ስለጸለየ ለሐዋርያትም ሥርዓተ ጸሎትን ስላስተማራቸው ዕለተ ጸሎት ሐሙስ ተብሎ ይጠራል፡፡

የሕማማት ሳምንት ከሰኞ እስከ አርብ፡ የጌታችን መከራና የድኅነታችን ጉዞየሕማማት ሳምንት በክርስትና እምነት እጅግ ታላቅና ቅዱስ ሳምንት ነው። ከሆሳዕና እሑድ ማግስት ጀምሮ እስከ ትንሳኤ ዋዜ...
06/04/2026

የሕማማት ሳምንት ከሰኞ እስከ አርብ፡ የጌታችን መከራና የድኅነታችን ጉዞ

የሕማማት ሳምንት በክርስትና እምነት እጅግ ታላቅና ቅዱስ ሳምንት ነው። ከሆሳዕና እሑድ ማግስት ጀምሮ እስከ ትንሳኤ ዋዜማ ድረስ ያለው ይህ ጊዜ፣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ድኅነት ሲል የተቀበላቸውን መከራዎች፣ ሕማማትና ስቅለት የምናስብበት ወቅት ነው። በተለይም ከሰኞ እስከ አርብ ያሉት ቀናት እያንዳንዳቸው የራሳቸው የሆነ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪክና ትርጉም ስላላቸው፣ በታላቅ ሥርዓትና ተመስጦ ይከበራሉ።

የየቀናቱ ዝርዝር ትርጉም
#ሰኞ (የአንጽሖተ መቅደስ ቀን)
ይህ ቀን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እየሩሳሌም ቅድስት መቅደስ በመግባት፣ በዚያ ይሸጡና ይለውጡ የነበሩትን ሁሉ “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፤ እናንተ ግን የሌቦች ዋሻ አደረጋችሁት” በማለት ያስወጣበትና መቅደሱን ያነጻበት ቀን ነው። (ማቴዎስ 21:12-13)

ምሳሌነቱ፡ ልባችን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መሆኑን እና ከኃጢአትና ከርኩሰት ልናነጻው እንደሚገባ ያስተምረናል።

#ማክሰኞ (የጥያቄ ቀን)
ጻፎችና ፈሪሳውያን፣ የካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች “በምን ሥልጣን እነዚህን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ?” ብለው ኢየሱስ ክርስቶስን የጠየቁበት ቀን ነው። እርሱም በምሳሌዎች አስተምሯቸዋል፣ ብዙ የመከራ ምሳሌዎችንም ተናግሯቸዋል። (ማቴዎስ 21:23)

ምሳሌነቱ፡ የክርስቶስ ሥልጣን ከሰማይ የመጣ መሆኑን እና እኛም ለፈቃዱ ልንገዛ እንደሚገባን ያስገነዝበናል።

#ረቡዕ (የምክር ቀን)
የአይሁድ ካህናትና ሹማምንት ክርስቶስን እንዴት በተንኮል እንደሚይዙትና እንደሚገድሉት የመከሩበት ቀን ነው። በዚህ ዕለት ይሁዳ አስቆሮቱ በሰላሳ ብር አሳልፎ ለመስጠት ከጠላቶቹ ጋር ተስማምቷል። (ማቴዎስ 26:14-16)

ምሳሌነቱ፡ በክፋትና በተንኮል የምናሴረው ሴራ፣ ለውድቀትና ለክህደት እንደሚዳርግ ያሳየናል።

#ሐሙስ (ጸሎተ ሐሙስ)
ይህ ቀን እጅግ ታላቅና ጥልቅ ትርጉም ያላቸው ኩነቶች የተፈጸሙበት ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻው እራት ላይ የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብ ትህትናን አስተምሯቸዋል። ምሥጢረ ቁርባንን (የሥጋውና የደሙ ምሥጢር) መሰረተ። በጌቴሴማኒ የአትክልት ስፍራ የመጨረሻውን ጸሎት ጸለየ። (ዮሐንስ 13:1-17፣ ማቴዎስ 26:17-30)

ምሳሌነቱ፡ የክርስቶስን ትህትና፣ የእግዚአብሔርን ፍቅርና ምሕረት፣ እንዲሁም የጸሎትን አስፈላጊነት ያስተምረናል።

#አርብ (የስቅለት ቀን)
ይህ የሕማማት ሳምንት ማጠቃለያና ታላቅ ቀን ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአይሁድ ፍርድ ቤት ፍርዱ ተወስኖበት፣ ተገረፈ፣ ተሰደበ፣ የምራቅ መተፊያ ሆነ፣ ቀላውን ጐበዝ ሰገደለት፣ የመከራ ዘውድ ደፋ፣ በመጨረሻም በቀራንዮ ተራራ ላይ ተሰቀለ። ለሰው ልጆች ድኅነት ሲል ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ሰጠ። (ዮሐንስ 19)

ምሳሌነቱ፡ የእግዚአብሔርን ታላቅ ፍቅር፣ የኃጢአትን ከባድነትና የድኅነትን ዋጋ ያስገነዝበናል።

ለምን ይከበራል?
የክርስቶስን መከራና ስቅለት ለማሰብ፡ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ፍቅር ሲል የተቀበላቸውን ስቃይና መከራ፣ ግርፋትና ስቅለት በጾምና በጸሎት፣ በስግደትና በተመስጦ ለማሰብ።

ለንስሐና ለሥርየት፡ በዚህ ሳምንት ራሳችንን ከኃጢአትና ከክፋት አርቀን፣ በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ፣ የኃጢአት ሥርየትን ለመለመን።

የድኅነትን ምሥጢር ለመረዳት፡ የሰው ልጅ ከኃጢአትና ከሞት ቀንበር የዳነበትን መንገድ፣ የእግዚአብሔርን ታላቅ ፍቅርና ምሕረት ለመረዳት።

ዋና ዋና ምንጮች
መጽሐፍ ቅዱስ፡ በተለይም የአራቱ ወንጌላውያን (ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ፣ ዮሐንስ) የመጨረሻዎቹ ምዕራፎች።

ግብረ ሕማማት፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በሕማማት ሳምንት ብቻ የሚነበብ፣ የጌታን መከራ በዝርዝር የሚተርክ መጽሐፍ።

የቤተክርስቲያን ታሪክና ትውፊት፡ ከሐዋርያት ጀምሮ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው የሊቃውንት ትርጓሜ።

ይህ የሕማማት ሳምንት በጾምና በጸሎት፣ በተመስጦና በንስሐ እንድናሳልፍ፣ የጌታችንን መከራና ስቅለት በማሰብ የድኅነትን ምሥጢር እንድንረዳ፣ የእግዚአብሔር ፍቅርና ምሕረት በልባችን እንዲሰርጽ፣ ራሳችንን ለንስሐና ለሥርየት እንድናዘጋጅ ረዳታችን ይሁን።

✞       በሰሙነ  ሕማማት  ይህንን  አድርጉ    ✞         ( በሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ )                ————————————          ለኹሉም እንዲዳረስ ሼ...
06/04/2026

✞ በሰሙነ ሕማማት ይህንን አድርጉ ✞
( በሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ )
————————————
ለኹሉም እንዲዳረስ ሼር ይደረግ !

ሰሙነ ሕማማት አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለም ሁሉ ቤዛ ሆኖ ተላልፎ መሰጠቱን የምናስታውስበት ሳምንት ነው።

ይህንን ምክንያት በማድረግ የሥርዓት ለውጥ ሲደረግ ሲመለከቱ ግራ የሚጋቡና ሥርዓተ አምልኮውን በሚገባ ከመከታተል ይልቅ ሥርዓት የጣሱ እየመሰላቸው የሚጨነቁ ስላሉ ልናደርገው የሚገባንን እጽፍላችኋለሁ።

1️⃣. በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ብሎ ፊትንና መላ ሰውነትን በትዕምርተ መስቀል {በመስቀል ምልክት} ማማተብ አይከለከልም። ከካህን እጅ ቡራኬ አንቀበልም በካህኑ እጅ ያለውን መስቀል አንሳለምምና ማማተብም የለብንም በሚል ፍልስፍና ካልሆነ ማማተብ ክልክል ነው ተብሎ የተጻፈበት ቦታ የለምና።

2️⃣. የሚከለከል ጸሎት የሌለ መሆኑን አውቃችሁ ያስለመዳችሁትን ጸሎት በትጋት ጸልዩ። መሥዋዕት ካለመሠዋታችን ቅዳሴ ካለመቀደሳችን በቀር በዚህ ሳምንት ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጀምሮ እስከ ሊቃውንት ድርሳናት ድረስ በቤተ ክርስቲያን የማይጸለይ ጸሎት የለምና።

3️⃣. ሰላምታ መስጠት ከጸሎተ ሐሙስ ዕለት በቀር አልተከለከለም፤ እሱም ቢሆን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በይሁዳ ሰላምታ ተላልፎ መሰጠቱን ለማስተዎስ እንጅ ሌላ የተለየ ምክንያት ስለሌለው በመርሳት ወይም በሌላ ከድፍረት በተለየ ምክንያት ሰላምታ ያቀረበላችሁን ሰው ልታስደነግጡና ትልቅ ኃጢአት እንደሠራ አድርጋችሁ ልታስጨንቁት አይገባም።

4️⃣. “በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ” ብሎ መጻሕፍትን ማንበብ ወይም ሌላ ሥራን መጀመር ይቻላል። ስመ እግዚአብሔር መጥራት የምንከለከልበት ጊዜ መቸም የለምና።

5️⃣. የጌታችንን ሕማሙንና ሞቱን የሚያስታውሱ መጻሕፍትን በማንበብና በመስማት ጊዜአችንን መወሰን ይገባናል።

6️⃣. በዚህ ሳምንት ተድላ ደስታን ሲያደርጉ መገኘት ከአይሁድ ጋር እንደ መተባበር የሚያስቆጥር ስለሆነ አብዝቶ በመብላትና በመጠጣት፣ ያማረውንና ጌጠኛውን ልብስ በመልበስ፣ ባልና ሚስት በምንጣፍ በመገናኘት እንዲሁም በልዩ ልዩ ምክንያት ከምናደርጋቸው ተድላ ደስታዎች መራቅ ይገባናል። ቅዱሳን በዘመናቸው ሁሉ ባሰቡት ጊዜ የሚያስጨንቃቸውን የክርስቶስን መከራ እያሰብን ለጥቂት ጊዜም እንኳን ቢሆን የክርስቶስን መከራ በሰውነታችን ማሰብ ይገባናል።

የተቻለው እንደ ጴጥሮስ የራሱን ኃጢአት እያሰበ እንደ ማርያም መግደላዊት የክርስቶስን ሞት እያዘከረ ሊያለቅስ ይገባዋል።
በወዲያኛው ዓለም ከማልቀስ የሚያድነን ዛሬ የራሳችንን ኃጢአት አስበን የክርስቶስን ሞት አዘክረን የምናለቅሰው ለቅሶ ነው እንጅ ዛሬ ከተደሰትን ደስታችንን በዚህ ዓለም ማድረጋችን አይደለምን?

7️⃣. በተቻለን መጠን በቤተ ክርስቲያን መዋል ይገባናል፤ ሕማማተ መስቀልን የሚያስታውሱ መጻሕፍት የሚነበቡበት ሳምንት ስለሆነ ነው። ነገር ግን በልዩ ልዩ ምክንያት በቤተ ክርስቲያን መዋል እንኳን ባይቻላችሁ ባላችሁበት ቦታ ሁናችሁ እየዋሻችሁ በሐሰት የከሰሱትን፣ እየቀማችሁ ልብሱን የገፈፉትን፣ ሰው እየደበደባችሁ በጅራፍ የገረፉትን፣ በወንድሞቻችሁና በእኅቶቻችሁ ላይ እየፈረዳችሁ በክርስቶስ ላይ የፈረዱበትን፣ በሰዎች ላይ እየተዘባበታችሁ የተዘባበቱበትን፣ በሳቅና በሽንገላ ሰውን እየሸነገላችሁ ሽንገላ በተሞላበት ሰላምታ ጌታውንና መምህሩን አሳልፎ የሰጠ ይሁዳን ልትመስሉ አይገባም።

ይልቁንም በአይሁድ እጅ ተላልፎ ቢሰጥም ንጹሓ ባሕርይ መሆኑን በማመን እስከ ቀራንዮ የተከተሉትን ደቀመዛሙርት ልትመስሉ ይገባል። እግራችሁ በመቅደሱ ውስጥ ባይቆምም ልባችሁን ከመቅደስ ልታወጡት አይገባም። እያዘናችሁ ባላችሁበት ቦታ ዋሉ።

8️⃣. በቤታችሁም ሆነ በቤተ ክርስቲያን አብዝታችሁ ስገዱ። ስለሁላችንም ቤዛ የሚሆን ክርስቶስ በፊታችን መስቀል ተሸክሞ ሲወድቅ እያያችሁት ትቆማላችሁን? አይሁድ ገፍተውት አንድ ጊዜ ወደ ምድር በወደቀ ጊዜ ለወደቀው መውደቅ ዘመናችንን ሙሉ ብንወድቅ ብንነሣ ውለታ መክፈል እንችል ይመስላችኋል?
ቅዱሳን ሳያቋርጡ ሲሰግዱ የሚኖሩት ክርስቶስ በፊታቸው በአይሁድ እጅ እየተገፋ መስቀሉን እንደተሸከመ ሲወድቅ በዓይነ ሕሊናቸው ስለሚያዩት ነው።
በስንክሳር ተጽፎ የምናገኘው ዜና ሞታቸው እየሰገዱ ሳሉ ሞት ነፍሳቸውን ከሥጋቸው ለይቶ እንደሚወስዳትና ለስገደት ታጥቀው እንደተንበረከኩ እንደሚገኙ ይነግረናል። የተሰቀለውን ክርስቶስን የሚያስብ ሰው ለሰውነቱ ዕረፍትን አይሻም።

9️⃣. ከሁሉም ሰው ጋር ፍቅርን አድርጉ። ሰውን ለመውደድ ምክንያት አታብጁ። ክርስቶስ አሳልፎ የሰጠውን ይሁዳን “ወዳጄ” ብሎ ሲጠራው አትሰሙትም?

እግዚአብሔርን አንተን ያለ ምክንያት እንደ ወደደህ አንተም ያለ ምክንያት ሰውን መውደድ ልመድ። ክርስቶስ አንተን ጠላቱ ሆነህ ሳለ ፍቅርን ካላጎደለብህ ለጠላትህ ፍቅርን አታጉድልበት።

ክርስቶስ ይሁዳን ‘’ወዳጀ’’ ብሎ ከጠራው አንተም ይሁዳዎችህን ወዳጀ ብለህ ጥራቸው። አውቃለሁ ጠላትን መውደድ መራራ ሐሞትን ከመጠጣት በላይ መራራ ነው። ነገር ግን እኔም ለይሁዳዎቻችን ፍቅርን እንስጥ ማለቴ መራራ ሐሞት የጠጣ ክርስቶስን እንድንመስለው ነው።

1️⃣0️⃣. ለሁሉም መስጠት በምትችሉት መጠን ስጡ እንጅ አትቀበሉ። ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነውና በመስጠታችሁ ብፁዓን ተብለው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ከሚገቡት ትቆጠራላችሁ።

ምናልባትም የምትሰጡት ገንዘብ ባይኖራችሁ ዕዳ ይሆንባችሁም ቢሆንም ገንዘብ ለሰጧችሁ ባለጠጎች የምትሰጡት ጸሎት ሊኖራችሁ ይገባል። ከምንጊዜውም የበለጠውን ስጦታ የተቀበልንበት ሳምንት መሆኑን እያሰባችሁ አንዳች የምጸጡት ሥጋዊም ሆነ መንፈሳዊ ስጦታ የሌላችሁ ባዶዎች እንዳትሆኑ ተጠንቀቁ።

ከሁሉ በላይ የሆነውን ስጦታ የጌታን ሥጋና ደም እነሆ ተቀብለናል።

ክርስቶስ መድኃኒነ
መጽአ ወሐመ በእንቲአነ
ወበሕማማቲሁ ቤዘወነ‼

( ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ )
የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት የሊቃውንት ጉባዔ ሰብሳቢ
የዐራቱ ጉባዔያት ምስክር መምህር

[  ]♥♥♥ ሆሣዕና ማለት የዕብራይስጥ ቃል ነው፤ “ሆሻአና” ሲባል ትርጒሙም “አቤቱ አኹን አድን” ማለት ነው፤ ይኽ በዓለ ሆሣዕና ከ9ኙ ዐበይት የጌታ በዓላት ውስጥ ሲኾን ኪሩቤል ሱራፌል በ...
04/04/2026

[ ]
♥♥♥ ሆሣዕና ማለት የዕብራይስጥ ቃል ነው፤ “ሆሻአና” ሲባል ትርጒሙም “አቤቱ አኹን አድን” ማለት ነው፤ ይኽ በዓለ ሆሣዕና ከ9ኙ ዐበይት የጌታ በዓላት ውስጥ ሲኾን ኪሩቤል ሱራፌል በፍርሀት በረዐድ ኹነው ዘፋኑን የሚሸሙት ጌታ በትሕትና በአህያና በውርንጫይቱ በትሕትና ተቀምጦ እየተመሰገነ ወደ ቤተ መቅደስ የገባበት፣ የዘካርያስ ትንቢት የተፈጸመበት፣ ሕዝቡ ዘንባባ ይዘው የዘመሩበት፣ ሕፃናት በንጹሕ አንደበታቸው ሆሣዕና ብለው ያመሰገኑበት ታላቅ በዓል ነው፡፡

♥♥♥ ይኽም ታሪክ በ4ቱ ወንጌላት ላይ ሲጻፍ በማቴ 21፡1 ላይ “ወደ ኢየሩሳሌምም ቀርበው ወደ ደብረ ዘይት ወደ ቤተ ፋጌ ሲደርሱ፥ ያንጊዜ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለት ላከ” ይላል፡፡

♥♥♥ ቤተ ፋጌ ማለት የበለስ ቤት ማለት ሲኾን ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ በሚወስደው መንገድ አቅራቢያ ያለች ትንሽ መንደር ናት፤ ኹሉን ዐዋቂ የኾነው ጌታም ጴጥሮስንና ዮሐንስን “በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፥ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከርሷ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ” በማለት እንደ ማዕምረ ኅቡአትነቱ (የተሰወረውን ዐዋቂነቱ) በመንደሯ ውስጥ ስለታሰሩት አህያና ውርንጫ አስቀድሞ ይነግራቸዋል፡፡

♥♥♥ በተናቀች ግርግም በቤተልሔም በተወለደ ጊዜ ላምና አህያ ትንፋሻቸውን እንደገበሩለት፤ አኹንም በሰዎች በተናቀች አህያ በጌትነት ተቀምጦ እንዲመሰገንባት መርጧታል፡፡

❤❤❤ በልደቱ ማንም ያልገባባት የማይገባባት የሕዝቅኤል የታተመች መቅደስ የተባለች ዘላለማዊት ድንግል እመቤታችንን እንደመረጠ ዛሬም በሆሣዕና ማንም ሰው ያልተቀመጠባት አህያን ከውርንጫዋ ጋር እንዲያመጡ አዘዘ።

♦ ከዚያም “ማንም አንዳች ቢላችሁ ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ፤ ወዲያውም ይሰዳቸዋል” በማለት የኹሉ ጌታ ርሱ መኾኑን አመለከታቸው፤ በተሰጣቸው ሥልጣነ ክህነት የሕዝቡንም የአሕዛቡን ኀጢአት የማሰር የመፍታት ሰማያዊ ሥልጣነ ክህነት የተሰጣቸው ሐዋርያትን የሕዝብ ምሳሌ የኾነችውን አህያይቱንና የአሕዛብ ምሳሌ የኾነችው ውርንጫዋንም እንዲያመጡ አዟቸዋልና።

♥♥♥ ሊቁ ጀሮምም፡- “ደቀ መዛሙርቱ አህያይቱንና ውርንጫይቱን ለመፍታት ኹለት ኾነው መላካቸው ለሕዝብም ለአሕዛብም መላካቸው ያመለክታል፡፡”

♥♥♥ ሊቁ አምብሮስ፡- “አህያየቱን ለመፍታት ማንም አይከለክላችኁም ብሎ መላኩ ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ የሰጣቸው የማሰር የመፍታት ሥልጣን ሰማያዊ መኾኑን ያመለክታል፡፡” በማለት ልዩ ምስጢርን አስተላፎበታል።

♥♥♥ አምጥተው “ልብሳቸውንም በእነርሱ ላይ ጫኑ”፤ በአህያዋና በውርንጫዋ ላይ ኮርቻ ሳይኾን ልብስ ማድረጋቸው ኮርቻ ይቈረቊራል ልብስ ግን አይቈረቊርምና የማትቈረቊር ሕግ ሠራኽልን ሲሉ። ዳግመኛም ልብስ በአካል ያለውን ኀፍረት እንዲሰውር አንተም በደላችንን የምትሰውርልን ይቅር ባይ ነኽ ሲሉ፡፡ በተጨማሪም ልብስ በልጅነት ይመሰላልና የተገፈፍነውን የጸጋ ልብሳችን (ልጅነትን) ትመልስልናለህ ሲል፨

♥♥♥ ቅዱስ ኤፍሬም ይኽነን ሲተረጉም "ልብሳቸውን አውልቀው ያነጠፉለት ሰዎች አሮጌውን ማንነታቸውን ትተው ዐዲሱን ልብስ ክርስቶስን መልበሳቸውን ያስረዳል። ሐዋርያ ጳውሎስ “አሮጌውን ሰውነት አስወግዳችሁ አዲሱን ሰው ልበሱት” እንዳለው (ኤፌ.4፣23) ይኸውም ጥምቀት ነው" ይላል።

♥♥♥ ከኢየሩሳሌም እስከ ቤተ መቅደስ 16 ምዕራፍ ሲኾን መተርጒማነ ሐዲስ በትርጓሜ ወንጌል ላይ እንደሚገልጹት 14ቱን ጌታ በእግሩ ሲኼድ 2ቱን በአህያዋ፤ በውርንጫዋ 3 ጊዜ ቤተ መቅደሷን ዞሯል፡- 14ቱ በእግሩ መኼዱ የ10ሩ ቃላት 4ቱ የ4ቱ ኪዳናት ምሳሌ፡፡ 2ቱ በአህያዋ መጓዙ የፍቅረ እግዚአብሔርና የፍቅረ ቢጽ፤ 3ቱን በውርንጫዋ ተቀምጦ ቤተ መቅደሱን መዞሩ የ3ትነቱ የአንድነቱ ምሳሌ ነበር፡፡

♥♥♥ ጌታ ንጉሠ ነገሥት ሲኾን፤ ኪሩቤል ሱራፌል ዙፋኑን በፍርሀት በረአድ የሚሸከሙት 24ቱ ካህናተ ሰማይ ዙፋኑን በፍርሀት የሚያጥኑለት ርሱ በትሕትና የዋህ ኾኖ በተናቁት በአህያና በውርንጫይቱ ላይ ተቀመጠ፤ ይኽም የተናቁትን ሊያከብር እንደመጣና፤ በየዋሀን ምእመናን ልቡና እንደሚያድር ለማሳወቅ በነርሱ ተቀመጠ። በተጨማሪም መተርጉማን እንዳመሰጠሩት በአህያ የተቀመጠ አባሮ እንደማይዝ ሸሽቶ እንደማያመልጥ ርሱም ካልፈለጉት እንደማይገኝ ከፈለጉት እንደማይታጣ በምስጢር አመለከታቸው፡፡

♥♥♥ በተጨማሪም አህያ ሲፈጥራት በጀርባዋ ላይ ትእምርተ መስቀል ያላት ናትና ትእምርተ መስቀል ያለባት እእርሷ እንድትፈታ ማዘዙ ከ5 ቀን በኋላ በመስቀል ተሰቅሎ በሲኦል የታሠሩትን የሰው ልጆችን ነጻ ሊያወጣ መጥቷልና አህያን መርጧታል፨

♥♥♥ ቅ.ዮሐንስ አፈወርቅ፡- ስለዚኽ ነገር በትርጓሜ ወንጌሉ ላይ “እነዚኽ እንስሳት መላውን የሰው ልጅ ይወክላሉ፡፡ ኹለቱም አህያ መኾናቸውም የሰው ልጅ ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት የነበረውን አኳኋን የሚያስረዳ ነው፡፡ ምክንያቱም አህያ በኦሪቱ ዘንድ ንጹሕ እንስሳ አይደለችም፤ ብዙ ክብደት ያላት የማትወደድ እንስሳ ናት፤ ደካማ ናት፡፡ ሰውም እንደተናገርን ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት እንዲኽ ነበረ፡፡” በማለት አመስጥሯል፡፡

♥♥♥ ሊቁ ቅ. ቄርሎስ ዘእስክንድርያም፡- “ፈጣሬ ኵሉ እግዚአብሔር ሰውን በምድር ላይ ጠቢብ አድርጐ ፈጥሮት ነበር፡፡ ማሰብና ማሰላሰል የሚችል ፍጥረት አድርጐ ፈጥሮት ነበር፡፡ ሰይጣን ግን አታለለው፡፡ ምንም እንኳን ሰው በሥላሴ አምሳል ቢፈጠርም መልኩን አበላሸው፡፡ ፈጣሬ ኵሉ እግዚአብሔርን ማወቅ ተሳነው፡፡ ክፉው ሰይጣን ሰውን እንስሳ እስኪመስል ድረስ ክብሩን አዋረደው፡፡ መዝሙረኛው ዳዊት፡- “ሰውስ ክብሩን አላወቀም፤ የሚጠፉ እስሳትን መሰለ” ያለውም ስለዚኹ ነው (መዝ.49፡12)፡፡ በመኾኑም አህያይቱ ክብራቸውን አጥተው ተዋርደው የነበሩትን እስራኤል ዘሥጋን ትመስላለች፡፡ እስራኤል ከሕጉ ጥቂት ነገርን ያውቃሉ፡፡ ከነቢያትና ከቅዱሳንም ትንሽ ያውቃሉ፡፡ ከኹሉም በላይ ደግሞ ወደ አሚን የሚጠራቸውን ክርስቶስን አልታዘዙትም፡፡ “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” ሲላቸውም እንደ አህያይቱ በድንቁርና ተይዘው እንደነበረ ሲገልጥላቸው ነው፡፡ ውርንጫይቱ ደግሞ አሕዛብን ትወክላለች፡፡ ውርንጫ እኽልን ለመጫን እንደማታገለግል ኹሉ አሕዛብም ማኅደረ እግዚአብሔር ከመኾን ርቀው ነበርና፡፡” በማለት ገልጿል፡፡

♥♥♥ ያን ጊዜ ከሕዝቡም እጅግ ብዙዎች ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ ይኽንም ማድረጋቸው ስንኳን አንተ የተቀመጥኽባት አህያ መሬት መርገጥ አይገባትም ሲሉ ነበር። እንስሳዋ እንኳን ጌታ ቢቀመጥባት እንዲህ ክብር ያገኘች ከሆነ ያደረባቸው ቅዱሳንማ የሚገባቸው ክብር ምን ያህል ይሆን? ይልቁኑ 9 ወር ከ5 ቀናት በማሕፀኗ የተሸከመችው ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ ሰው የሆነውን አምላክ የወለደችው የቅድስት ድንግል ማርያም ክብርማ እጅጉን ታላቅ ነው።

❤❤❤ ሌሎችም ከዛፍ ጫፍ ጫፉን እየቈረጡ በመንገድ ላይ ያነጥፉ ነበር። ይኽም ዘንባባ ብዙ ምሳሌ ያለው ነው፤ ይኸውም በእስራኤል ያለው ሰሌን፣ ተምር፣ ዘይት ነበርና ያነን ቈርጠው አመስግነውታል፤ ይኽም ምሳሌነት ያለው ነው፤ ይኽም ሰሌን እሾኻማ እንደኾነ ትእምርተ ኀይል ትእምርተ መዊእ አለኽ ሲሉ ነው፤ እሳት ለብልቦ ይተወዋል እንጂ እንደማያቃጥለው ባሕርይኽ አይመረመርም ሲሉ ነበር፡፡

♥♥♥ ዳግመኛም ከሰሌን ዝንጣፊ ጋር ተመሳሳይ ተምር ይዘዋል ይኽም ተምር ልዑል ነው አንተም ልዑለ ባሕርይ ነኽ ሲሉ፤ ፍሬው አንድ እንደኾነ አንተም ዋሕደ ባሕርይ ነኽ ሲሉ፡፡ በእሾኽ የተከበበ ነው ባሕርይኽ አይመረመርም ሲሉ ነበር፡፡

♥♥♥ የዘይት ዛፍ ነው ቢሉ ዘይት ጽኑዕ እንደኾነ ጽኑዐ ባሕርይ ነኽ ሲሉ፤ ብሩህ ነው ብሩሀ ባሕርይ ነኽ በትምህርትኽም የሰውን ልቡናን ታበራለኽ ሲሉ፤ ዘይት መሥዋዕት እንደሚኾን መሥዋዕት ትኾናለኽ ሲሉ ነበር፡፡

♥♥♥ “የሚቀድሙትም ሕዝብ የሚከተሉትም ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር” በማለት በአርያም መድኀኒት እንደኾነና እግዚአብሔር አብ “የምወድደው ልጄ ይኽ ነው” ብሎ መስክሮለት የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ መርገመ ሥጋ
መርገመ ነፍስን የሚያርቅ በረከተ ሥጋን በረከተ ነፍስን የሚያድል መኾኑን ኹሉም መሰከሩለት፡፡

♥♥♥ በእጅጉ የሚደንቀው የ40 ቀን የ80 ቀን ሕጻናት የፈጠራቸው ጌታ በአህያና በውርንጫ ተቀምጦ ባዩት ጊዜ በንጹሕ አንደበታቸው አንደታቸው ረቶላቸው ጌታን ዘንባባ በመያዝ ሲያመሰግኑ በእጅጉ ይደንቅ ነበር፤ ነገር ግን ጸሐፍት ፈሪሳውያን ያደረገውን ድንቃ ድንቅ በመቅደስም ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ እያሉ የሚጮኹትን ልጆች ባዩ ጊዜ፥ ተቈጥተው እነዚህ የሚሉትን አትሰማምን? አሉት፤ ኢየሱስም፦ እሰማለሁ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን ለራስህ አዘጋጀህ የሚለውን ቃል ከቶ አላነበባችሁምን? በማለት በሕጻናት እንደሚመሰገን የነርሱም ጌታ መኾኑን ከዳዊት መዝሙር በመጥቀስ ነገራቸው፡፡

♥♥♥ ሊቁ ያዕቆብ ዘሥሩግ ሰለዚኽ ምስጢር ሲገልጸው ፡- “ፍቅርኽ ከዘባነ ኪሩብ አውርዶ በአህያ ጀርባ ላይ እንድትቀመጥ አስገደደኽ፡፡ ብዙ ዐይንና ብዙ ገጽ ካላቸው ከሰራዊተ መላክእት ይልቅ በዲዳዋ አህያ ትመሰገን ዘንድ ወደደክ፡፡ በሰማይ ሰራዊት ሠረገላ ተቀምጠኽ ክብርኽን ማሳየት አልወደድክም፤ በውርንጫላይቱ ላይ ተቀምጠኽ ወደ ሰማይ ሰራዊት መኼድን መረጥክ እንጂ፡፡ በአርያም እሳታውያን የሚኾኑ ኪሩቤል ያመሰግኑኻል፤ በምድርም ሕፃናት ይዘምሩልኻል፡፡ በአርያም ብርሃናውያን መላእክት በብርሃን ክንፋቸው መንገድኽን ያነጥፉልኻል፤ በምድርም ደቀ መዛሙርትኽ ልብሳቸውን አንጥፈው መንገድኽን አስተካከሉ፡፡ ወዮ! አርያማዊ ሲኾን ምንም ሳይንቀን ይጐበኘን ዘንድ ከአባቱ መጣ፡፡ ርሱም በገዛ ፈቃዱ ሰው እስከ መኾን ደርሶ መጣ፡፡ በአህያ ላይ ተጭኖም ይጐበኘን ዘንድ መጣ፡፡ ነቢዩ ዘካርያስ የመንፈስ ቅዱስን እንዚራ ይዞ በደስታ ትንቢትን ለመናገር ይቻኰላል፡፡ እየደረደረም የጽዮንን ልጅ ይጠራታል፡፡” በማለት አስተምሯል፡፡

♥♥♥ የምስጋና ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያዋና በውርንጫዋ ላይ ተቀምጦ ሕፃናትን ጨምሮ ዘንባባ ሰሌን በያዙት ኹሉ “ሆሣዕና በአርያም” እየተባለ እየተመሰገነ ወደ ቤተ መቅደስ የገባበትን ታላቁን በዓል ከኹሉም ዓለም አስበልጣ በታላቅ ክብር የምታከብርና የምታስተምረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡

♥♥♥ ይኸውም ታላቁ የምስጋና ዕለት ሊደርስ ሲቃረብ ስንዱዋ እመቤት አስቀድማ በቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ የቊርባን ምስጋና፦
✍ “ቦአ ኀቤሃ እግዚአ አጋዕዝት ወመናፍስት እንዘ ይጼዐን ዕዋለ አድግ ትሑት…” (የአጋዕዝትና የመናፍስት ጌታ በተዋረደ አህያ ግልገል ተቀምጦ ወደ ርሷ ገባ፤ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ብሩክ ነው፡፡ አንተም የአማልክት አምላክ የእስራኤልም ንጉሥ እግዚአብሔር ቡሩክ ነኽ እያሉ ለሚያመሰግኑ ሕፃናት ኹሉ ጌትነቱን አሳየ፤ የሆሳዕናን ዑደት ለነርሱ ለደቀ መዛሙርቱ አሳየ፤ ቡርክ ርሱ በታላቅ ቃል እየጮኻችኊ ሆሣዕና በአርያም በሉ አላቸው፤ ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሳዕና በአርያም፤ ከመድኀኒትነቱ የተነሣ ከዚኽ አስቀድሞ ያልተደረገ ከዚኽም በኋላ የማይደረግ ተአምራትንና መንክራትን አሳየ፤ ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሳዕና በአርያም... ) በማለት መድኀኒትነቱን ስትሰብክ፤ ካህናትና ምእመናንም በአንድ ድምፅ በዚያ ዘመን የምስጋና ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በተመሰገነበት በዚኽ ልዩ ምስጋና “ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም” እያሉ በመዘመር፤ ፈጣሪያቸው ክርስቶስን ያመሰግናሉ፡፡

♥♥♥ ከዚያም በዋዜማው፦
✍ “በዕምርት ዕለት በዓልነ ንፉሑ ቀርነ በጽዮን ወስብኩ በደብረ መቅደስየ እስመ ይቤ ዛቲ ዕለት በዓለ እግዚአብሔር ሆሣዕና በአርያም ቡሩክ አንተ ንጉሠ እስራኤል” (በታወቀች በበዓላችን ዕለት በጽዮን መለከትን ንፉ፤ በመቅደሴ ተራራም ስበኩ ይኽቺ ዕለት የእግዚአብሔር በዓል ናት፤ በአርያም መድኀኒት የተባልኽ የእስራኤል ንጉሥ አንተ ቡሩክ (መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን የምታርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን የምታድል) ነኽ) በማለት ልዩ ምስጋናዋን ጀምራ እስከ ሌሊቱ ድረስ በልዩ ምስጋና እየሰበከችው በኋላም ቤተ መቅደሱን በውርጫዋ ተቀምጦ እንደዞረ በአራቱ መኣዝን የጌትነቱ ወንጌል እየተነበበ፤ ካህናቱን ምእመናንም በእጃቸው የዘንባባ ዝንጣፊን ይዘው “ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ያመሰግኑታል፡፡

  ?+።።።።።።።።።።።።።+።።።።።+ገብርኤል ማለት “ እግዚእ ወገብር” - የእግአብሔር አገልጋይ ማለት ነው። ፍጥረታት መፈጠር በጀመሩበት በዕለተ እሑድ እግዚአብሔር መላእክትን ከፈጠራቸው ...
27/03/2026

?
+።።።።።።።።።።።።።+።።።።።+

ገብርኤል ማለት “ እግዚእ ወገብር” - የእግአብሔር አገልጋይ ማለት ነው። ፍጥረታት መፈጠር በጀመሩበት በዕለተ እሑድ እግዚአብሔር መላእክትን ከፈጠራቸው በኋላ ተሰወራቸው መላእክትም “ መኑ ፈጠረነ፡ ማን ፈጠረን ” ሲሉ ዲያብሎስ እኔ ፈጠርኳችሁ ብሎ መላእክት በተረበሹ ጊዜ “ የፈጠረንን አምላካችን እስክናውቅ በያለንበት ጸንተን እንቁም ” ብሎ ያረጋጋቸው መልአክ ነው። በዚህም ምክንያት ጌታ “ በእንተዝ ይደልዎ ከመ ይጹር ዜናሃ ለማርያም ” እንዲል ሥጋዌውን ለድንግል እንዲያበስር አድሎታል።
ከዚህም በኋላ ደጋግ ሰዎችን ለመርዳት የሚወጣ የሚወርድ ሆኗል።

🔺ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ በእግዚአብሔር ፊት የሚቆመው ታማኝ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

🔺በተረዳኢነቱና በአማላጅነቱ በክርስቲያኖች ዘንድ ይወደዳል፡፡

🔺 ያዘኑትን ለማጽናናት የምሥራች ለመንገር ከእግዚአብሔር ወደ ምእመናን የሚላክ ይህ ቅዱስ ገብርኤል ነው።

🔺ሳጥናኤል ሥላሴን በካደ ጊዜ መላእክትን በቃሉ ያጽናናቸው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱና በእግዚአብሔር ፊት የሚቆም ይህ ገብርኤል ነው፡፡

🔺በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለሚኖሩ ብርሃን የገለጸና የሰበከ ይህ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

🔺የነቢያትን ትንቢት የፈጸመ፤የክርስቶስን ልደት ለድንግል ያበሰረ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ዳንኤልን ከአናብስት ያዳነው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ሠለስቱ ደቂቅን ከእቶን እሳት ያዳነቸው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ወደ ዘካርያስ የተላከ የዮሐንስን ልደት ያበሰረ ይህ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ወደ ዮሴፍና ወደ ኒቆዲሞስ የተላከ
ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣን ከእቶን እሳት ያዳናቸው ይህ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ሰብአ ሰገልን በኮከብ ምልክት የመራቸው
ይህ ገብርኤል ነው፡

🔺ድንግል ማርያምና ሕፃኑን ክርስቶስን በምድረ በዳ በስደታቸው የመራ ይህ ገብርኤል ነው፡

🔺የብርሃን ራስ ወርቅ የተቀዳጀ ገብርኤል ነው፡፡

🔺የአሸናፊና የኃይል መልአክ ገብርኤል ነው፡፡

🔺ነበልባላዊ ዖፈ ሰማይ ገብርኤል ነው፡፡

❗️

  👉 የስሙ ትርጓሜ ‹አክሊል› የሆነው በሕገ ወንጌል የመጀመሪያ ሊቀ ዲያቆናትና ቀዳማዊ ሰማዕት የተባለ ቅዱስ እስጢፋኖስ ‹‹ሊቀ ዲያቆናት›› ከመባሉ በፊትም በመጀመሪያ ሐዋርያና ካህን ነበር...
26/03/2026



👉 የስሙ ትርጓሜ ‹አክሊል› የሆነው በሕገ ወንጌል የመጀመሪያ ሊቀ ዲያቆናትና ቀዳማዊ ሰማዕት የተባለ ቅዱስ እስጢፋኖስ ‹‹ሊቀ ዲያቆናት›› ከመባሉ በፊትም በመጀመሪያ ሐዋርያና ካህን ነበር፤ ከዚያም ዲያቆን ሆኖ ተሾሟል፤ ይህም ጥቅምት ፲፯ ቀን ነው፡፡

ቀዳሜ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ:-

👉 በሐዲስ ኪዳን በክርስትና ምክንያት ሰማዕትነትን ከተቀበሉ መካከል የቀደመ፣ ክብር፣ ቅዱስ ሰማዕት

👉 በመጽሐፍት እውቀቱ የተለየ በመንፈስ ቅዱስ የተቃኘ ሊቀ ዲያቆናት

👉በከሳሾቹ ፊት ሞትን ሳይፈራ የክርስቶስን እውነት የመሰከረ፣ በብርሃን የተመላለሰ ሐዋርያ

👉ልክ እንደ ክርስቶስ ጠላቶቹ በሀሰት ክስ ተነስተው ሲገድሉት ይቅርታን የለመነላቸው ቅዱስ

👉 ታላቅ ሐዋርያ፣ ሰባኪ፣ ጻድቅ፣ ሰማዕት የሆነው ቅዱስ እስጢፋኖስ በዚህ ቀን በየወሩ ይታሰባል

የሊቀ ዲያቆናት ወቀዳሜ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ ምልጃና በረከት ይደርብን።

ገብር ኄር፡ የዐቢይ ጾም 6ተኛ ሳምንትበመ/ር ጌታቸው በቀለየዐቢይ ጾም ስድስተኛው ሳምንት ገብር ኄር ተብሎ ይጠራል፡፡ገብር ኄር ተብሎ በሚጠራው  ሳምንትም ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቅድስት ቤተ...
21/03/2026

ገብር ኄር፡ የዐቢይ ጾም 6ተኛ ሳምንት
በመ/ር ጌታቸው በቀለ

የዐቢይ ጾም ስድስተኛው ሳምንት ገብር ኄር ተብሎ ይጠራል፡፡

ገብር ኄር ተብሎ በሚጠራው ሳምንትም ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቅድስት ቤተክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት፣ የሚነበበው ወንጌል ገብር ኄርን የሚያወሳ ነው።
በዚህ ሳምንት እግዚአብሔር አምላክ ለሰው ሁሉ የሚያገለግልበት ጸጋ መሰጠቱን፣ ቅን አገልጋዮች ስለሚቀበሉት ዋጋ፣ ሰነፍ አገልጋዮች ስለሚጠብቃቸው ፍርድ ይሰበካል፡፡

“ጌታውን ያስደሰተው አገልጋይ ታማኝና ቸር አገልጋይ ነው፤ ቸር አገልጋይ ማን ነው?” እያሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይዘምራሉ፤ በቅዳሴው ደግሞ የማቴዎስ ወንጌል ፳፭፥፲፬-፴ ይነበባል።
ገብር ኄር ምን ማለት ነው?
ገብር ኄር ማለት ቸር፣ ታማኝ አገልጋይ፣ ቅን ታዛዥ አገልጋይ ማለት ሲሆን ዕለቱ የታማኝ አገልጋዮች ዋጋና የጌታውን ፈቃድ ፈጽሞ የተገኘ አገልጋይ የሚመሰገንበት ዕለት ነው፤ “መልካም አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ” እንዲል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መልካም ሠርተው ለታመኑ የሚያደርገው በረከት የሚገለጥበት ነው።
ታማኝ አገልጋይ ማነው?
ታማኝ አገልጋይ ማለት ከራሱ በላይ ለሌሎቹ የሚያስብ፣ ሁሉን ለእኔ ብቻ የማይል፣ ስግብግብ ያልሆነ፣ ለእውነት የሚፈርድ፣እውነትን እና ቅንነትን ያስቀደመ ያ ሰው ታማኝ አገልጋይ ነው ምንያቱም ከራሱ የበለጠ ለሌላው ያስባልና።

በቅዱስ መጽሐፍ በታማኝነት ያገለገሉ ሲሾሙ እናያለን፡፡ ለአብነትም ያህል እግዚአብሔር አምላክ “አገልጋዬ ዳዊትን እንደ ልቤ የታመነ ሰው ሆኖ አገኘሁት” በማለት እንደገለጸው ዳዊት የተገኘውና የተቀባው በታማኝነቱ ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሴፍም የታማኝነት ተምሳሌት ነው፡፡

በቤተ ጲጥፋራም በታማኝነቱ ጌታ ሆኖ ሳለ፤ ከጌታው ሚስት የቀረበለትን የዝሙት ፈተና “እንዴት በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአትን እሠራለሁ?” በማለት በጽናት አልፏል፡፡

በመከራና በእስር ቤትም ታማኝነቱ ስላልተለየው በመጨረሻ ግብጽን እንዲመራ በትልቅ ሹመት ተሸሟል፤ “በጥቂቱ የታመነ በብዙ ይሾማል” እንዲል /ማቴ.፳፭፥፳፬/፡፡
ጌታችን በማቴዎስ ወንጌል /ማቴ.፳፭፥፲፬-፴/ ባስተማረው ምሳሌ፤ አንድ ባለጸጋ ወደ ሩቅ ሀገር ሲሄድ ለሦስት አገልጋዮቹ እንደ አቅማቸው ለአንዱ አምስት፣ ለአንዱ ሁለት፣ ለአንዱ ደግሞ አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡

አምስት መክሊት የተሰጠውም ለፍቶ፣ ጥሮ፣ ግሮ ሌላ አምስት መክሊት እንዳተረፈ፤ ሁለት መክሊት የወሰደውም ሌላ ሁለት መክሊት አተረፈ፡፡

ማትረፍ ማለት የተሰጠንን መንፈሳዊ ጸጋ ለሌሎች ማካፈልና በዚያም ከራሳችን አልፈን ለሌሎች የድኅነት ምክንያት መሆን ማለት ነው፡፡

ጌታቸው ሲመለስም “ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” የሚል የዘላለም ክብር ተሰጣቸው፡፡ አንድ መክሊት የወሰደው ግን በስንፍናና በቸልታ ምድርን ቆፍሮ የጌታውን መክሊት እንደቀበረው ይነግረናል።
የመክሊቱ ባለቤት
የመክሊቱ ባለቤት አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ባለ አምስት፤ ባለ ሁለትና ባለ አንድ መክሊት የተቀበሉት በጥምቀት ጸጋ መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉ፤ተምረው የሚያስተምሩ መምህራን ናቸው፡፡ የስጦታው መለያየት መበላለጥን ለማሳየት ሳይሆን የአንዱ ጸጋ ከሌላው እንደሚለይ የሚያጠይቅ ነው፤ “መንፈስ ቅዱስ አንድ ሲሆን ስጦታው ልዩ ልዩ ነው፡፡ ጌታም አንድ ሲሆን ልዩ ልዩ አገልግሎቶች አሉ” /፩ቆሮ ፲፪፥ ፬/፡፡

ባለ አምስትና ባለ ሁለት መክሊት የተባሉት አገልጋዮች ለጌታቸው ታማኝ የነበሩ፤ በተቀበሉት መክሊት ወጥተው፣ ወርደው አትርፈው የተገኙ ናቸው፡፡ በተሰጣቸው መክሊት መጠን በእምነት በማገልገላቸው ሁለቱም ገብር ኄር (ቸር አገልጋይ) የሚል የክብር ስም ተሰጥቷቸዋል፡፡

ባለ አንድ መክሊት የተባለው ዐላውያን ነገሥታት፤ ዐላውያን መኳንንት እሳት ስለት አሳይተው ቢያስክዱኝ፣ መናፍቃን ተከራክረው ቢረቱኝ፣ ምላሽ ቢያሳጡኝ፣ ሃይማኖቴን ቢያስቱኝ ብሎ ከማገልገል ይልቅ ሃይማኖቱን የማያስተምርና የማይመሰክር ነው፡፡

“ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤ በሰው ፊት የሚክደኝን ግን እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እክደዋለሁ” ብሏል፤ /ማቴ.፲፥፴፪/፡፡

ስለዚህ በተሰጠን መክሊት በተባለ ጸጋ በሰው ሁሉ ፊት በማገልገል ልንመሰክር ይገባል፡፡
ባለጸጋ የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን መክሊቱም ለእያንዳንዳችን የሚሰጠንን የተለያየ ጸጋ ያመለክታል። “ከብዙ ዘመን በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው” ማለቱ ከብዙ ዘመን በኋላ በዕለተ ምጽአት ለሁሉም በአገለገለው አገልግሎት ዋጋ ለመስጠት የሚመጣውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይገልጻል።
ከጊዜያት በኋላ ባለ ጸጋው ያበደራቸውን ገንዘብ ውጤት ማስገኘቱን ለማወቅና ለመቆጣጠር መጣ፡፡ ገንዘቡ ምን ሁኔታ ላይ እንዳለ እያንዳንዳቸውን ጠየቀ፡፡

አምስት መክሊት የወሰደው ዐሥር፣ ሁለት መክሊት የወሰደው አራት አድርገውና ጌታቸው ከሰጣቸው መክሊት እጥፍ ለጌታቸው ስለሰጡ ጌታቸውም “አንተ ታማኝ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ ታምንሃል በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታ ደስታ ግባ።” እያለ በየተራ አስገባቸው።

ያ አንድ መክሊት የወሰደው ባሪያ ግን ወደ ጌታው ፊት ቀርቦ “ጌታዬ ሆይ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንክህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ ፈራሁም ሄጄ መክሊትህን በምድር ቀበርኩት እነሆ መክሊትህ አለ።” አለው። የተሰጣቸውን መክሊት በእጥፍ ያተረፉት እግዚአብሔር የሰጣቸውን ጸጋ በሚገባ የተጠቀሙ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ስዎች ሲሆኑ “ወደ ጌታህ ደስታ ግባ።” ማለቱም ትዕዛዙን እና ቃሉን ጠብቀው በተሰጣቸው ጸጋ ያገለገሉ ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉ ሲል ነው።

የተሰጠውን መክሊት መሬት ቆፍሮ የቀበረው እግዚአብሔር የሰጠውን ጸጋ ሳይጠቀምበት አምላኩን የሚያማርር በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ሰነፍ በመሆኑ፤ መጨረሻውም ጥርስ ማፋጨት ስቃይና ጽኑዕ ጨለማ ባለበት ሲዖል መግባት መሆኑ ያመለክታል።
የአገልጋዮቹ ጌታም ከሄደበት ሲመለስ አገልጋዮቹን የሰጣቸውን መክሊት ምን እንዳደረጉበት ጠየቃቸው፡፡ ሁለቱ አገልጋዮች (አምስት እና ሁለት የተቀበሉት) በተሰጣቸው መክሊት ማትረፋቸውን ሲናገሩ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን እንዲሠራበት የተሰጠውን መክሊት እንደቀበረው ተናገረ::

መቅበሩም ብቻ ሳይሆን “አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ ሰለፈራሁም ሄድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ” በማለት በጌታው ላይ የማይገባ ንግግርን ተናገረ፡፡

የአገልጋዮቹ ጌታም አደራቸውን ጠብቀው በተሰጣቸው መክሊት ለማትረፍ የደከሙትን አገልጋዮች በጥቂቱ በመታመናቸው በብዙ ሲሾማቸው መክሊቱን የቀበረውን ያንን ኀኬተኛ አገልጋይ ግን በተግሣጽ ወደ ውጪ እንዲያወጡት አዘዘ፡፡
የምሳሌው ትርጉም
ጌታችን በዚሀ ምሳሌ አድረጎ ያስተማረን አንድ፣ አምስት እና ሁለት መክሊት የወሰዱት አገልጋዮች ፍጽምት ትምህርትን ተምረው፣ አላዊያን እሳት ስለት አሳይተው እንዳያስክዱኝ ብለው ወደ ኋላ ሳይሸሹ መናፍቃን ተከራክረው ምላሽ ቢያሳጡን ብለው ሳይፈሩ መክረው አስተምረው ቅዱስ ጴጥሮስ ቀሌምንጦስን፣ ቅዱሰ ጳውሎስ ጢሞቴዎስን እንዳወጡ ሁሉ፤ መክረው ዘክረው ምእመናንን ከክህደት ከጥፋት የሚጠብቁ ታማኝ አገልጋዮች ምሳሌ ናቸው፡፡
በተሰጠን መክሊት ምን አተረፍን?

ዛሬ ሁላችንም መክሊት ተቀብለናል፡፡ ግማሾቻችን አምስት መክሊት፣ ግማሾቻችን ሁለት እንዲሁም አንድ መክሊትን (ጸጋን) ከጌታችን ተቀብለናል፡፡

የግማሹ ጸጋ መዘመር ነው፤ የግማሹ ማስቀደስ ወይም መቀደስ፣ የሌላው ደግሞ ማስተማር ወይም መማር ይሆናል፡፡ ብቻ “የአንዱ ኮከብ ክብር ከሌላው ኮከብ ክብር ይበልጣል” እንዲል መጽሐፉ የአንዳችን ጸጋ ከሌላችን ጋር ይለያያል፡፡ ነገር ግን ሁሉም በተሰጠው ጸጋ ማትረፍ ይጠበቅበታል፡፡

መምህሩ አስተምሮ፣ ተማሪውም ተምሮ፣ ዘማሪውም ዘምሮ፣ አስቀዳሹም አስቀድሶ፤ ሁሉም በተሰጠው ጸጋ ጌታችን ሲመጣ ከእያንዳንዱ ትርፍን ይፈልጋል፡፡

ሁላችንም ከመላእክት ጋር በምናመሰግነበት በሰማያዊው መንግሥት አንተ በትንሹ የታመንክ በጎ አገልጋይ በትልቁ እሾምሀለሁ ብሎ እንዲያስገባን ያቺ የምንጠየቅባት ቀን ከመድረሷ በፊት ዛሬ በተሰጠን ጸጋ ልናተርፍበት ይገባል፡፡
እንደ ማጠቃለያ
እግዚአብሔር የልጅነት ጸጋ በመስጠት ለእኛ ያለውን ፍቅር አሳይቶናል፡፡ አምስትና ሁለት መክሊት የተቀበሉ ለጌታቸው ታማኝ የነበሩ፣ በተቀበሉት መክሊትም መከራን ታግሰውና በእምነት በማገልገላቸው ሁለቱም ቸር አገልጋይ የተባሉ ናቸው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለው አገልጋይ እምነት የጎደለው ተጠራጣሪ ነበርና ማትረፉን ሳይሆን መክሰሩን ብቻ የሚያስብ፣ የተፈጠረበትን ዓላማና የተሰጠውን ተልእኮውን ያልተረዳ ሰው ነበር፡፡ እኛም በጥምቀት ዳግም የተወለድነውና በመስቀሉም የዳንነው ተልኮአችንን ተረድተን በመልካም ሥራና በታማኝነት እንድናገለግል ነው፡፡ ጌታ ለአንዱ አምስት፣ ለአንዱ ሁለት፣ ለአንዱ አንድ መክሊት የሰጠው እንደየአቅማቸው ነው፡፡

ጌታችን ለእኛም ለእያንዳንዳችን እንደ አቅማችን የአገልግሎት ጸጋ ሰጥቶናል፡፡ በአገልግሎት ጸንተን ልንገኝ ይገባል፡፡ ጻድቃን ሰማዕታት በታማኝ አገልግሎታቸው ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋልና፡፡
እያንዳንዳችን ራሳችንን ማየት አለብን፡፡ ጸጋችንን እናውቃለን? ለማወቅስ እንሻለን? በተሰጠን ጸጋ አትርፈናልን? ካላተረፍን ለምን? ከእግዚአብሔር ዘንድ ጸጋ ያልተቀበለ የለም፤ ሰው ጸጋውን አለማወቁ አልተቀበለም፤ ጸጋ የለውም አያሰኝም፡፡

ከሁሉ አስቀድመን ጸጋ እንደ ተሰጠን ማመን ይጠበቅብናል፡፡ በዚህም ምክንያት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር የሰጠንን ጸጋ ችላ እንዳንል ለማነቃቃት በየዓመቱ በዚህ ሳምንት የእነዚህን አገልጋዮች ታሪክ ታስታውሰናለች::

ይህም ብቻ ሳይሆን የአገልጋዮቿ ፍጻሜ እንደተመሰገኑት እንደ ሁለቱ አገልጋዮች እንዲሆንም ወደ አምላኳ ትጸልያለች፡፡ አምላካችን እግዚአብሔር በቸርነቱ ይጎብኘን፣ በተሰጠን መክሊት የምናተርፍ፣ ለሀገር ለቤተክርስቲያን የምንጠቅም፣ በቅንነትና በታማኝነት የምናገለግል ደገኛ አገልጋዮች ያድርገን፡፡ ጌታችን ለታማኝ አገልጋዮቹ ያዘጋጀውን “ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” የሚለውን የክብር ቃል ለመስማትና መንግሥቱን ለመውረስ ያብቃን፡፡ አሜን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
የእግዚአብሔር ቸርነት የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም
አማላጅነት አይለየን፡፡ አሜን፡፡
ዋቤ መጻሕፍት
✍️ መጽሐፍ ቅዱስ
✍️ መጽሐፈ ድጓ
✍️ መጽሐፈ ግጻዌ
✍️ ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜ
✍️ ጾም ምጽዋት
✍️ የቤተክርስቲያን ታሪክ በኢትዮጵያ

Address

Addis Ababa

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ገዳሜ ተዋህዶ_Gedame tewahido posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share