07/09/2026
ቅዱስ ሩፋኤል ከሰባቱ ሊቃነ-መላእክት አንዱ ነው። ሊቀ-መላእክትነቱም ❝መናብርት❞ በሚባሉ መላእክት ላይ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ዙፋን ፊትም ለማማለድና ትእዛዝ ለመቀበል ከሚቆሙት ሰባቱ መላእክት ሦስተኛው መልአክ ሩፋኤል ነው፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል ለሰውና ለእንስሳት ርኅሩኅ መልአክ ነው፡፡ በርኅራኄውም የሰው ልጆች ምሕረትን፣ ብዕልና ክብርን ያገኙ ዘንድ ይልቁንም የመካኖችን ማኅፀናቸውን ይፈታ ዘንድ ወላጆችም ያለ ጽኑ ምጥ ይወልዱ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ቀርቦ እንደሚለምን በቅዱሳን ዘንድ በስፋት የታወቀ መልአክ ነው፡፡
በዕብራይስጥ ቋንቋ ❝ሩፋ❞ ማለት ጤና፣ ፈውስ፣ መድኃኒት፣ መስተፍሥሒ፣ ድንቅ ማለት ነው፡፡ ❝ኤል❞ ማለትም አምላክ ማለት ስለ ሆነ ሁለቱ ቃላት ሲጣመሩ ሩፋኤል የሚል ይሆናል፡፡ ይህም ከአምላክ የተሰጠ ድንቅ ፈውስ ማለት ነው፡፡
❝ስሙሂ ብሂለ ሩፋኤል መስተፍሥሒ ወመድምም ብሂል ወትርጓሜሁ ፈውሰ አምላክ ውእቱ — ሩፋኤል የተባለ ስሙ ደስ የሚያሰኝ ትርጓሜውም ድንቅ የአምላክ ፈውስ❞
— እንዳለ (ድርሳነ ሩፋኤል ዘጥር) እርሱም የሰዎች ነፍሳትን በምልጃው ለማዳን የተሾመ የዋህ መልአክ እንደ ሆነ ነቢዩ ሄኖክ:-
❝ሩፋኤል ፩ዱ እመላእክት ቅዱሳን ዘመናፍስተ ሰብእ — ከቅዱሳን መላእክት አንዱ ሩፋኤል በሰዎች ነፍሳት ላይ የተሾመ ነው❞
— (ሄኖ፮÷፫) ካለ በኋላ በሌላ አንቀጽ ሁለተኛውም በበሽታው ሁሉ ላይና በሰው ልጆች ቊስል ላይ የተሾመ ❝ቅዱስ ሩፋኤል ነው❞ በማለት ያስረዳናል (ሄኖ፲፥፲፫)።
የነፍሳት ጠባቂ ለመሆኑ መጽሐፈ ሜላድ ነፍሳትን ለመጠበቅ በሰዎች ነፍሳት ላይ ከተሾሙ ቅዱሳን መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው ይላል (መጽሐፈ ሜላድ ዘጥቅምት)
❝የነፍስ ጠባቂ ለሆነ ሩፋኤል ሰላምታ ይገባል
❞
— (ተአምኆ ቅዱሳን ዘሰሉስ) ቅዱስ ሩፋኤል ለሄኖክ መካነ ነፍሳትን እንዴት እንደ ሆነ ተርጕሞ አስረድቶታል።
ዳግመኛም ❝ሩፋኤል❞ ማለት ልቡናን ደስ የሚያሰኝ፤ ያዘኑትን የሚያረጋጋ፤ መፈውስ፣ የዋህ፣ ይቅር ባይ ማለት ነው፡፡
❝ወአንሰ ስምየ ሩፋኤል መስተፍሥሔ አልባብ የዋህ ወኄር ወመሐሪ ላዕለ ኀጥአን — የመላእክት አለቃ ሩፋኤልም ለሐዋርያት ስሜ ሩፋኤል ነው፤ ትርጓሜውም የዋህና ሰውን አስደሳች፤ ቸር ለኃጥአን ይቅር ባይ ማለት ነው፤ ኃጥአንን ስለበደላቸው ወደ እግዚአብሔር አላሳጣቸውምና፥ ነገርግን ስለ የዋህነቴና ስለ ማዳኔ የሰውንም ልጅ እጅግ ስለ መውደዴ ከኃጢአታቸው ተመልስው ንስሓ ይገቡ ዘንድ በዘመን ላይ ዘመንን እጨምርላቸዋለሁ አስፈጻሚ መላእክትንም እልክላቸዋለሁ❞
— እንዳለ ድርሳነ ሩፋኤል ዘጳጕሜን።
የሰማያትን መክፈቻ ስለያዘ ሕፃናትን ገና በናታቸው ማኅፀን ጀምሮ ይጠብቃቸዋል። ኃጢአተኞችን ለንስሓ እያበቃ በንስሐ የተመለሱ የቅዱሳን ነፍሳትን ወደ ገነት፤ ወደ መንግሥተ ሰማያት እንዲገቡም ያደርጋል፡፡ በወርኃ ጥር የሚነበብ ድርሳኑ እንዲህ ይላል:-
❝አዳም ሚስቱ ሔዋንን ዐወቃት፡፡ ያን ጊዜም የዲያብሎስ ሠራዊት ከሚስቱ ሔዋን ማኅፀን የአዳምን ዘር ያጠፉ ዘንድ በፅንስ በሽታ ተመስለው ተነሡ:: ስለዚህም እግዚአብሔር ሊቀ-መላእክት ቅዱስ ሩፋኤልን መርጦ ከሌሎች ይልቅ የሰውና የእንስሳን ማኅፀን ይፈታ ዘንድ ሥልጣንን ሰጠው:: ለደካሞች የሚያዝን፤ የሚራራ፤ የተበደሉትንም የሚበቀልላቸው ልዑል እግዚአብሔር ይኸን ሥልጣን ባይሰጥ ኑሮ ከዲያብሎስ ሠራዊት የተነሣ አጋንንት ሾተላይ፣ የሐኬት ቊራኝነት የተነሣ ይህ ዓለም ያለ ፍጥረት ምድረ በዳ ሆኖ በቀረ ነበር። ርጉም ዲያብሎስ ከኃጥአን ማኅፀን ከሚገኙ ልጆች በቀር ደጋግ ጻድቃን እንዲፈጠሩ አይሻም
ና።❞
ወስብሐት_ለእግዚአብሔር