17/05/2026
”
✍️ ሰው መሆን መታደል ነው ፡፡ ሰው መሆን እንደ እግዚኣብሔር የሚሠራ፣ እንደ እግዚኣብሔር የሚኖር፣ እግዚኣብሔርን የሚመስል የእግዚኣብሔር እንደራሴና ፍጥረታትን የሚያስባርክ፣ የፍጥረት ሁሉ የበላይ ፍጥረታት እግዚኣብሔርን የሚያዩበትና የፍጥረታት ዘውድ መሆን ማለት ነው፡፡
✍️ የሰው ሕብረቱ ከእግዚኣብሔር ጋር በመሆኑ ጥቃቅን ልዩነቶች አይበግሩትም ነበር፡፡ እግዚኣብሔራዊ ሕብረት መቸም ቢሆን በልዩነት ወይም በድንበር አያምንም፡፡ ይልቁንም “አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት” (ኤፌ:4፡5) በማለት ያስተምራል፡፡ ሰው የሆነ ሁሉ በዚህ መርሕ ሊሄድ ይገባዋል ፡፡ በዚህ በእኛ ዘመን በርካታ የልዩነት አጀንዳዎች ቢኖሩም እነዚህን ልዩነቶች አቻችሎ መኖር ትልቅነት ነው። ሁላችንም እንደምናውቀው በዓለማችን ብዙ የመቻቻል ትምህርቶች ቢኖሩም ሊቃውንቱን የአንድነት ሰባኪ እያስባሉ ከማለፍ ባሻገር ልዩነትን አላጠበቡም። ሰውነት ግን በየአደባባዩ ከሚሰጡ በርካታ ልፈፋዎች ይልቅ እርቅን የሚያበዛ፣ ልዩነት የሚያጠብና ፍቅርን የሚያነገሥ ነው።
✍️ ሰው መሆን አንተ የእርሱ እኔ የእነ አገሌ የሚለውን ሐሳበ አርቆ ሰውን በሰውነቱ ብቻ ወንድሜ ብሎ ማመንን የሚያጸናና መተባበርን የሚያጠነክር እንጂ በልዩነት ጎራ ላይ የሚንጠለጠል አይደለም ። ምክንያቱም “ከጥንት ግን እንዲህ አልነበርንም” ማቴ. 19፡8 ።
✍️ ጥንተ ተፈጥሯችን የሚነግረን የሰው ልጅ ብቻውን መኖር እንደማይችልና አንዱ የአንዱን ክፍተት በመሙላት መኖርን እንዲያዳብር ነው። ከዚህ የምንረዳው በጋራ መኖር፣ መሥራት፣ ማቀድና መፈጸም ለሰው ልጅ የተልእኮው አካል መሆኑን ነው። ብዙ ሰዎች ሁሉንም እኔ ልሥራው፣ እኔ ልመስገንበት ሲሉ ቢታዩም ለሚፈጠረው ክፍተት ኀላፊነት ካለመውሰዳቸውም ባሻገር በተፈለገው ልክ አፈጻጸሙ ግብ አይመታም።
✍️ በሀገራችን አባባሎች ውስጥም በጋራ መሥራት ምን ያህል ወሳኝ እንደሆነ ሲያጠይቁ "ከአንድ ብርቱ ሁለት መዳኒቱ፣ በአንድ እጅ ማጨብጨብ፣ አንድ እንጨት አይነድ አንድ እንጨት አይፈርድ፣ ተማክሮ ምን ያሉት ፣ጋን በጠጠር ይደገፋል" የሚሉና መሰል በርካታ ሐሳቦች መተባበር ምን ያህል ዋጋ እንዳለው የሚያሳዩ ናቸው። ትብብራችን ማሕበራዊ መስተጋብራችን ከመሆኑም ባሻገር ሀይማኖታዊ ግዴታችን ነው።
✍️ ይህንን ስንል ግጭትና ጠንሳሾቹ አይኖሩም እያልን አይደለም። በስነ-ፍጥረት እንደምናውቀው ውሃ ወደታች እንጂ ወደላይ አይፈስም ፡፡ ነገር ግን ሰው ሠራሽ መሳሪያዎችን በመጠቀም ወደ ላይ እስከ 300 ሜትር እንዲፈስ ማድረግ ይቻላል፡፡ ወደላይ መፍሰስ የውሃ ፀባይ ባይሆንም በሰው ሠራሽ ተፅዕኖ ምክንያት ያለ ፀባዩ ወደላይ ይፈሳል፡፡ እንደዚሁ ሁሉ የሰው ልጅም ከጥንት እንዲህ አልነበረም ፡፡ በአንዳንድ ሰው ሠራሽ አስተሳሰብ፣ መስተጋብርና ምልከታ ምክንያት ያለ ጸባያችን እንገፋፋለን። መገፋፋቱ የመጣው የተፈጥሮ ጸባያችን ሆኖ ሳይሆን ሰው ሠራሽ ምልከታዎች ተጽዕኖ ስላሳደሩብን ነው። ተፈጥሯችን ግን ፍቅር፣አንዱ ለአንዱ ሙላትና በረከት መሆን ነው።
✍️ የዚህ ዘመን ትልቁ ፈተና ደግሞ ሰው መሆን አለመቻል ብቻ ሳይሆን ለበረከት የራቀህ ሰው ለእርግማን ወደ አንተ የሚመጣ መሆኑ ነው። የልዩነቱ ተባባሪ ሊያደርግህ የሚጥረው ብዙ ነው። በልቡ የሳለውን እውነት አድርጎ ይጭንብሃል። ተፈጥሮ የጫነችብህን ፈተና ያቀልልኛል ያልከው ወንድምህ ራሱ ጫና ሊሆንብህ ሲሞክር ሰውነት ምን ያህል ዋጋው እየወረደ መሆኑ ይገባሀል።
✍️ ከጥንት ግን እንዲህ አልነበርንም። ተፈጥሯችንም ሆነ ታሪካችን ይህንን አይነግረንም። ዋሽቶ ማስታረቅን ባሕላቸው የነበሩ አባቶች ልጆች ሆነን ዋሽቶ ማጣላትን ያዳበርን መሆኑ እጅግ የሚደንቅ ነው። ዋርሳ መውረስ ድንበር ማፍረስ ነውር ነው ከሚል ማኅበረሰብ የተገኘን እኛ ዝሙትን ለማንገሥና ጽድቅ ለማልበስ ስንጥር አጀብ የሚያስብል ነው። ስርቆት ከእግዚአብሔር የሚያጣላ፣ በማሕበረሰቡ ዘንድ ነውር ነው እየተባልን ያደግን ዛሬ የስልጣኔ መገለጫ በሚመስል መልኩ ማየታችን እጅን በአገጭ የሚያስጭን ነው።
✍️ ሁላችንም የምናምነው ከጥንት እንደዚህ ያለነበርን መሆናችንና ወደፊት እንደዚህ የማንቀጥል መሆናችንን ነው። ወደ ቀልባችን ተመልሰን ሰው እንድንሆን እግዚአብሔር ይረዳን ዘንድ መጸለዩ ግን ግድ ነው።
✍️ ሰው መሆን ሲያቅተን ሰው ሆነህ ያዳንከን አምላካች ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በዘመናችን ሰውነት ጥያቄ ውስጥ ገብቷልና በተለመደው የትድግና ባሕርይህ ትፈውሰን ዘንድ መልካም ፈቃድህ ይሁንልን።
ሁላችንም ከጥንት በነበርንበት ልክ እንድትሠራን እንለምንሃለን!!! አሜን! አሜን! አሜን!!!
መጋቤ ሃይማኖት ጌታባለው አድማሱ (ሰባኬ ወንጌል)
ግንቦት ፱ ቀን ፪፻፲ወ፰ዓ.ም.
አዲስአበባ , ኢትዮጵያ
ውድ አንባቢያን ሐሳቤን በቅንነት እንድትረዱኝና ቢሆን የምትሉትን እንዲሁም ማለት አልነበረብህም የምትሉትን እንድትነግሩኝ በአክብሮት እጠይቃለሁ
ለተጨማሪ መረጃ የሚከተሉትን ይወዳጁልኝ።
1ኛ ፌስቡክ ገጽ ፦ https://www.facebook.com/share/1FgCQc8bfv/
2ኛ ዩቲዩብ ፦ https://youtube.com/?si=zZNtyMwXd_OF3k26
3ኛ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/?_t=ZM-8zuh8ovZtQh&_r=1
4ኛ ቴሌግራም ፦ https://t.me/GB2729
5ኛኢሜይል፦[email protected]