07/04/2026
ወሰን የሌለው የክርስቶስ ፍቅር
ፍቅር በሰው ልጅ መዝገበ ቃላት ውስጥ እጅግ ውድ እና ትልቅ ቃል ነው። ነገር ግን የሰው ፍቅር ሁል ጊዜ በሁኔታዎች የተገደበ ነው፤ የሰው ፍቅር ቢበዛ እስከሞት ይደርሳል፣ ከዚያ በኋላ ግን የለውም። የክርስቶስ ፍቅር ግን "ወሰን የሌለው"ነው፤ ምክንያቱም በሞትም፣ በመቃብርም፣ በኃጢአትም፣ በበደልም የማይገታ ፍቅር ነው።
1. ወደ ምድር ያወረደው ፍቅር ነው (ፊልጵስዩስ 2፡6-8)
የክርስቶስ ፍቅር የጀመረው በመስቀል ላይ አይደለም፤ የጀመረው ከሰማያዊ ክብር በመለቀቅ ነው። እርሱ የአምላክነት ክብር ነበረው፤ ነገር ግን ፍቅሩ እጅግ ስለበዛ "የባሪያን መልክ ይዞ"ወደ ምድር መጣ። ወሰን የሌለው ፍቅር ማለት እራስን ዝቅ ማድረግን የሚጠይቅ ፍቅር ነው። እግዚአብሔር በአንተ ሕይወት ውስጥ ጣልቃ የገባው፣ አንተን ለመፈለግ ከሰማይ ወደ ምድር በመውረድ ነው።
2. ፍቅሩ በደልን የሚጋርድ ፍቅር ነው (1ኛ ጴጥሮስ 2፡24-25)
"24 ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ፤
25 በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ። እንደ በጎች ትቅበዘበዙ ነበርና፥ አሁን ግን ወደ ነፍሳችሁ እረኛና ጠባቂ ተመልሳችኋል።"
የሰው ፍቅር በአንድ ሰው ላይ መጥፎ ነገር ሲሰራ ይቆማል። የክርስቶስ ፍቅር ግን እኛ "ኃጢአተኞች ሳለን"በዚያ ሁኔታችን ያፈቀረን ፍቅር ነው። ያ ፍቅር የእኛን መራራነት፣ የእኛን ዓመፅ እና የእኛን ስህተት ሁሉ በመስቀል ላይ ተቀብሎ በደሙ የሸፈነ ፍቅር ነው። ወሰን የሌለው ፍቅር ማለት በደልን የሚያሸንፍፍቅር ነው።
3. ፍቅሩ መቃብርን የሻረ ፍቅር ነው (ዮሐንስ 11፡25)
"ትንሳኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል።"የሰው ፍቅር በሞት ይሸነፋል። የክርስቶስ ፍቅር ግን ሞትን አሸንፏል። እርሱ የሞተው ፍቅሩ ስለተጠናቀቀ ሳይሆን፣ ለእኛ አዲስ ሕይወት ሊሰጠን ነው። ትንሳኤው ማረጋገጫው ነው! ፍቅሩ እስከ መቃብር ድረስ ተከትሎን፣ መቃብሩን ሰብሮ ህይወትን ሰጥቶናል። ወሰን የሌለው ፍቅር ማለት ለዘላለም የሚኖርፍቅር ነው።
4. ለምን ያህል ሰው? (ዮሐንስ 3፡16)
የክርስቶስ ፍቅር "ለተመረጡት ብቻ "ወይም "ለጻድቃን ብቻ "የተገደበ አይደለም። ዮሐንስ 3፡16 እንደሚለው "ዓለምን እንዲሁ ወዶአልና"።
~የአንተ ስህተት የክርስቶስን ፍቅር ከእርሱ ጋር ሊያለያይህ አይችልም።
~የአንተ መጥፋት የክርስቶስን ፍቅር ሊያሳጥረው አይችልም።
~የትም ብትሆን፣ ምን ብትሆን፣ የክርስቶስ ፍቅር ወሰን የለውም።
>ለዛሬው ቀን ጥሪ
ውድ ወዳጄ፣ ምናልባት በሰዎች ፍቅር ተስፋ ቆርጠህ ይሆናል፤ ወይም "እግዚአብሔር ይወደኝ ይሆን?"ብለህ ትጠይቅ ይሆናል። ዛሬ ይህ መልዕክት ላንተ ነው፡ የክርስቶስ ፍቅር ወሰን የለውም።
°የተጠራጠርክ ከሆነ:እርሱ ዛሬም አንተን ይፈልግሃል።
°የተጎዳህ ከሆነ:እርሱ ቁስልህን ሊጠግን ይፈልጋል።
°የራቅህ ከሆነ:የፍቅሩ እጆች አሁንም አንተን ለመቀበል ክፍት ናቸው።
ዛሬ ለዚህ ወሰን ለሌለው ፍቅር እጅህን ዘርግተህ "አዎ" በለው። እርሱ ሕይወትህን በአዲስ የፍቅር ብርሃን እንዲሞላው ፍቀድለት።