08/15/2026
በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን የ10 ዓመት፣ የ15 ዓመት፣ የ20 ዓመት፣ 40ኛ ዓመት ወይም 50ኛ ዓመት የምስረታ በዓል” እያሉ ማከበር የተለመደ አሰራር ሆኗል። ነገር ግን ይህ ልምምድ በአዲስ ኪዳን እውነት ሲመዘን ሙሉ በሙሉ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት የሌለው እና የክርስቶስን አካል እንደ ግል ድርጅት የመቁጠር ስህተት ነው።
ለመሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ቤተ ክርስቲያን ምስረታና እድገት ምን ያስተምራል? የሚከተሉትን ጠንካራ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች እንመልከት፦
ኢየሱስ ክርስቶስ "ቤተ ክርስቲያኔን እሰራለሁ" አለ እንጂ "የእገሌን ቤተ ክርስቲያን ትሰራላችሁ" አላለም (ማቴዎስ 16:18)። ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ደም የተዋጀች ሕያው አካል ነች (ሐዋርያት ሥራ 20:28)። አንድ ግለሰብ ወይም ፓስተር ህንፃ ስለተከራየ ወይም የራሱን ስብሰባ ስለጀመረ "የቤተ ክርስቲያኔ የምስረታ በዓል" ማለቱ፣ የክርስቶስ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን እንደ ግል ኩባንያ ወይም ንግድ ድርጅት የመቁጠር አደገኛ አካሄድ ነው።
በአዲስ ኪዳን ውስጥ ሐዋርያው ጳውሎስ፣ ጴጥሮስም ሆኑ ሌሎች ሐዋርያት የተከሏቸውን አብያተ ክርስቲያናት (የኤፌሶን፣ የቆሮንቶስ፣ የገላትያ ወዘተ) ዓመታዊ የምስረታ በዓል አላከበሩም።
የሐዋርያት ትኩረት የተጠናቀቀውን የክርስቶስን የጸጋ ወንጌል ማወጅ እንጂ፣ የአገልግሎታቸውን ዘመን ወይም የተቋማቸውን እድሜ ማክበር አልነበረም። ይህ አሰራር ከዓለማዊ ባህል ኮፒ ተደርጎ ወደ ቤተ ክርስቲያን የገባ ነው።
አብዛኞቹ የአኒቨርሰሪ ፕሮግራሞች ትኩረታቸው ወደ ፓስተሩ ስኬት፣ ወደ ህንፃውና ወደ ድርጅቱ እድገት የሚያደሉ ናቸው። ነገር ግን የወንጌል እውነት ማዕከል ክርስቶስ ብቻ ነው።
"ነገር ግን ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክህት ከእኔ ይራቅ" (ገላትያ 6:14)። የሰውን አገልግሎትና የተቋምን ዘመን ማክበር ትኩረትን ከክርስቶስ መስቀል ወደ ሰው ስራ ያዞራል።
መጽሐፍ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያንን የሚገልጻት እንደ "የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን" (1ኛ ጢሞቴዎስ 3:15) እና እንደ "የክርስቶስ አካል" (1ኛ ቆሮንቶስ 12:27) አድርጎ ነው።
የምስረታ በዓል የሚያስፈልገው ላለፈ ታሪክ ወይም ለሰዎች ድርጅት ነው። ሕያው የሆነችው ቤተ ክርስቲያን በየእለቱ በክርስቶስ ሕይወት የምትኖር እንጂ በዓመት አንድ ቀን የቀን መቁጠሪያ እየጠበቀች የምታከብር ተቋም አይደለችም።
📌ቤተ ክርስቲያን የተመሰረተችው በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል እና በጴንጤቆስጤ ቀን በመንፈስ ቅዱስ ወረደበት ቅጽበት ነው! ግለሰቦች የራሳቸውን ድርጅታዊ አኒቨርሰሪ ማክበራቸው አዲስ ኪዳናዊ መሠረት የለውም። በክርስቶስ ደም የተዋጀች ቤተ ክርስቲያን በየእለቱ ክርስቶስን ታከብራለች፣ ታስባለች፣ ትሰብካለች እንጂ እንደ ባልና ሚስት Anniversary እያለች ማክበር ይለባትም።
ጸጋ ይብዛላችሁ!
ጸጋዬ ግርማ